Welcome

"The thing that lies at the foundation of positive change, the way I see it, is service to a fellow human being." - Lech Walesa

Tuesday 13 November 2012

በደል ይረሳል ወይስ ይለመዳል

ይኸነው አንተሁነኝ
11-11-2012
በደል ይረሳል ወይስ ይለመዳል ወገን? ጉልበተኛው ወያኔ በጉልበቱ ተማምኖ በማን አለብኝነት እና በማን አህሎኝነት የምንኖርበትን ቦታና ፍላጎታችንን ሳይቀር ወስኖ በንቀት ረግጦ መግዛቱ ሳያንሰው፤ ህገመንግስታዊ መብታችን ይከበር፣ መንግስት ራሱ ላወጣው ህግ ይገዛ፣ መብታችንን ተጠቅመን የሰጠነው የምርጫ ድምጻችን ይከበር ብለው ጥያቄያቸውን ለማሰማት የወጡ ሰላማዊ ሰልፈኞችን እድሜ ዘመናቸውን ወስኖ፤ እንደፈለገ የሚያዛቸውን የአጋዚ ሰራዊት በመጠቀም በጠራራ ፀሐይ በሀገራችን የተለያዩ ከተሞች አውራ መንገዶች ላይ ያለርህራሄ ግንባር ደረታቸውን እየቀደደ እንደ ውሻ ሬሳ እንደ አልባሌ ያጣለበት ወርሃ ትቅምት እንሆ ሰባትኛ የሃዘን ዓመት ባተ።

ጨዋታ ያልጠገበው ህጻን ድንገት በጥይት አረር በግፍ ተመትቶ መውደቁንና ረዳት ማጣቱን ያየው ሌላው ከሱ ያልተሻለው ወንድሙ፣ በጁ ምንም ነገር አለመያዙን በንግግርና በምልክት እጆቹን አንስቶ እየገለጸ፤ ወንድሜን ለማንሳት ብቻ፣ ወንድሜን ለመርዳት ብቻ በማለት በልጅ ፍርሃቱና አንደበቱ እየማለና እየተገዘተ ወደ ወንድሙ ቢሮጥም የጠበቀው ግን እንዳሰበው አልነበረም። ሞቱ የተደገሰለት፣ አድሜው በወያኔ የተቆረጠለት ይህ ህጻን አሰከሬኑ የወንድሙን ሬሳ አቀፈ እንጅ እሱስ እንደፈለገው በህያው እጁ አላቀፈውም። ወንድሜ ይፈልገዋል ያለውን ርዳታ ሊለግስ እንደጓጓ፣ እንደተመኘና ይህንንም ለመፈጸም ወንድሙ ወደ ወደቀበት እንደሮጠ፤ በቃ አልተመለሰም እሱንም እንደወንድሙ የወንድሙ ገዳዮች አብረው ደፉት። ታዲያ ይሄ ይረሳል ወገን? ወይስ በእርግጥ ይለመዳል?

የእጃቸውን የመከራ ጥላሸት በቀሚሳቸው እየተረጉ እባካችሁ በኔ ይሁንባችሁ ባለቤቴ እናንተ እንደምትሉት አይነት ሰው አይደለም። እባካችሁ እስኪ ትንሽ ተረጋጉና አድምጡኝ ብለው መማጸናቸው ከአንድ ኢትዮጵያዊ የተከበሩ አማውራ ስለ ልጆቻቸው አባት የሚቀርብ በጣም ዝቅተኛው ልመና ሊሆን አይገባውም ነበር እንዴ? ይህ ግን ለወያኔ የመዳፈር ያህል ያስቀጣል ከዚያም ሲያልፍ ሂዎትን ታክል ተተኪ የሌላት ነገር ያስከፍላል። እናም የወያኔ አጋዚ ወታደር  ልመና ስለለመኑት ብቻ፣ ጥያቄ ስለጠየቁ ብቻ  ተከብረው በኖሩበት ልጆች ወልደው ባሳደጉበት በራቸው ላይ  ያለርህራሄ ደፍቷቸው ግዳይ ጥሎ አስከሬናቸውን ተሻግሮ በኩራት የሄደው። ታዲያ ይሄ እንዴት ይረሳል? እንዴትስ ይለመዳል?

ቸር አውለኝ ብሎ በሰላማዊ መንገድ መንግስትን ሊያናግር ችግሩንም ሊያሰማ የወጣን ሰልፈኛ ሀገርን፣ ህዝብን፣ ሃይማኖትን ሊያዋርድ ባህር አቋርጦ ድንበር ተሻግሮ እንደ ገባ ወራሪ ጠላት በሩምታ ተኩስ ቆሉት፣ እያሳደዱ ደበደቡት። በመቶዎች የሚቆጠር ምስኪን ህዝባችንን ፈጁት፣ ወርሃ እሸት- ጥቅምት የህዝብ እሸት ታጨደባት፣ የልጅ አዋቂ የሴት ወንድ አስከሬን ተከመረባት፣ የከተሞች ዋና ዋና መንገዶቻችን በደም ታጠቡ፣ አስፋልቶች በረጋ የሰው ደም ተሞሉ። የአእዋፍ ጫጫታ፣ የግርማ አራዊት ድንፋታ ጸጥ እረጭ አሉ። በምትኩ የመለስ ዜናዊ የማያባራ ማስፈራሪያና ያጋዚ ሰራዊት የእንቅስቃሴ እርምጃ ምድሪቱን አራዷት። ከዚያም በያቅጣጫው አፈሳ ሆነ፣ ትርምስ በረታ፣ የእናት የልጆች የጭንቀት የማንቋረር ደምጾች እንደገና አየሩን ሞላው። 

በሁለተኛው ዓለም ጦርነት ወቅት በግፈኛው ሂትለር በጀርመንና ባካባቢው የአውሮፓ አገሮች ሲሳደዱና ወደ እስር ቤት ሲጋዙ እንደነበሩት እስራኤላዊያን፤ ምስኪን ኢትዮጵያዊያንም በራቸው እየተሰበረና ቤታቸው እየተበረበረ ተሳደዱ ተጋዙ በአስር ሽዎች በሚቆጠር አሃዝም የሚገመት ህዝብ በሀገሪቱ በተለያዩ ቦታዎች የሚገኙትን እስር ቤቶችን ሁሉ ሞሉት፤ ልክ የዛሬ ሰባት አመት በወርሃ ጥቅምት 1997 ዓ/ም። ግን ለምን? ራሱ ወያኔ ባመጣው ጨዋታ ስለተረታ? በእርግጥ ይህ ነበር ዲሞክራሲ? የህዝብ የበላይነት የሚባለውስ የት ደረሰ? ዎያኔዎች ታገልንለት ሞትንለት የሚሉት የህግ የበላይነትም የይስሙላ እንደነበር በዚህ የከፋ ድርጊታቸው ተረጋገጠ።

እንደ አቤል ደም በጽርሃርያም የሚጮኸው የዚህ ሁሉ ምስኪን ኢትዮጵያዊ ደም የእሪታና ዋይታ ድምጽ በጆሯችን እየደወለ ማባነኑና ማስበርገጉ ሳይለቀን፣ እንዳልነበር ሆኖ ተቦዳድሶ የወደቀው የወገኖቻችን ገላ ከዓይነ ህሊናችን ሳይጠፋ እና እዥ እንደማያጣው እንደ ጎርምጥ የቆላ ቁስል ልባችን ደምቶ ጨርሶ እያዠ ባለበት ባሁኑ ሰአት፤ ደብል ዲጅት አድገት፣ ትራንስፎርሜሽን፣  ወጤት ተኮር ፣ የህዳሴ ግድብ ግንባታ፣ የታላቁ  መሪ ራዕዮች ሳይበረዙና ሳይከለሱ ማስፈጸም የሚሉና ሌሎችንም በመደርደር በብልጣብልጥነት ጉዳትን የማስረሳት፣ ጥቃትን የማዘናጋት እርምጃዎች በዎያኔዎች ሲወሰዱ እያስተዋልን እንገኛለን።

ታዲያ የወጋ ቢረሳ የተወጋ ይረሳል እንዴ? እስኪ ላንዲት ደቂቃ ወደ ህሊናችን እንመለስ ወገን፤ በእርግጥ ሽብሬን እና የ1997 ዓ/ም ሰማእታትን የደፏቸው ተጠይቀዋል? ለፍርድስ ቀርበው የስራአቸውን አግኝተዋል? ከዚያም ወዲህ እኮ ተጨማማሪ ጥፋቶችና ግድያዎች እየተፈጸሙ ነው። በቅርቡ በገርባ ቀበሌ የተፈጸመውን የሰላማዊ ሙስሊሞችን ጭፍጨፋ እንደ ቅርብ ምሳሌ  መውሰድ ይቻላል። ወገን ያላለቀ የተጀመረ ታሪክ አለን። የአካል ቁስል ያለበት ሰው ቁስሉ አስካልዳነ ድረስ ሁሌም በሽተኛ እንደሆነው ሁሉ ይኸው እኛም ላለፉት ሰባት አመታት ይህን የህሊና ቁስል ተሸክመን አለን። እንበላለን እንጠጣለን እንወጣለን እንገባለን ቁስላችን ግን ሁሌም ያመረቅዛል እንጂ አይድንም፤ ልንላመደውም አንችልም ቁስል አይለመድምና። ትልቁ መፍትሄ ግን መታከም ነው ። ወያኔ ከተከለብን ከዚህ የህሊና ቁስል የምንፈወሰው የበሽታውን ምንጭ ወያኔን በውድም ሆነ በግድ አሽቀንጥረን ስንጥለው ብቻ ነው። ያኔ አዲስ የሚፈጠር የአካልም ሆነ የህሊና ቁስል አይኖርም። ከዚህ በፊት ወንጀል የሰሩትንም ለፍርድ ለማቅረብ መብት ይኖረናል። የምንወዳትን ሀገራችንን ብቃት ላለው መሪ ለማስረከብ ህጋዊ መሰረት ለመጣል እንችላለን። ስለዚህም ኑ እንተባበርና የገፉንን ገፍተን ለህዝባችን ዲሞክራሲን እናስፍን ዲሞክራሲያዊነትን በማስፋፋት ዲሞክረሲያዊ መሪዎችን እናምርት።

No comments:

Post a Comment