Welcome

"The thing that lies at the foundation of positive change, the way I see it, is service to a fellow human being." - Lech Walesa

Saturday 25 August 2012

የኩማ አስተዳደር በይፋ ድንኳን ተክሎ ለቅሶ ተቀመጠ

ነሀሴ ፲፱ (አስራ ዘጠኝ ) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-የኩማ አስተዳደር በተለምዶ ማዘጋጃ ቤት ተብሎ በሚጠራው ቅጥር ግቢ ውስጥ የጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊን  ሞት አስመልክቶ ሁለት ትልልቅ ድንኩዋኖችን በግቢው ውስጥ ተክሎአል። አስተዳደሩ ከፌዴራል መንግስት በተለየ የከተማዋ ነዋሪዎች ሐዘናቸውን የሚገልጹበት ቦታ ያስፈልጋል በሚል ሁለት ትልልቅ ድንኩዋን ትላንት የተከለ ሲሆን አንዳንድ ሰዎች ሐዘናቸውን በለቅሶ በመግለጽ ላይ ናቸው፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘም በይፋ ባይገለጽም የአቶ መለስ ሞት ከተሰማ በኃላ የአስተዳደሩ ልዩ ልዩ ቢሮዎች ምንም ዓይነት አገልግሎት መስጠት ያቆሙ ሲሆን ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችንም በቢሮአቸው ማግኘት አስቸጋሪ ሆኖአል፡፡

አንድ አስተያየት ሰጪ በመንግስት ተቋም ደረጃ ድንኩዋነወ ተክሎ ሕዝብ እንዲያለቅስ ማነሳሳት ተራ የፖለቲካ ትርፍ ፍለጋ ካልሆነ በስተቀር ፋይዳ የሌለው ተገቢ ያልሆነ ተግባር ነው ሲል ተችቶታል፡፡አስተያየት ሰጪው አያይዞም ሕዝብ በራሱ መንገድ በየቤተ እምነቱ ሄዶ ሐዘኑን የሚገልጽበት ጸሎትም የሚያደርግበት ሥርዓት ቀድሞም ያለ መሆኑን በማስታወስ እስከ ቀብሩ ድረስ ከ15 ቀናት በላይ አገር ሐዘን ላይ እንዲቀመጥ ማድረግ ኃላፊነት ከሚሰማው አመራር የሚጠበቅ አይደለም ብሎአል፡፡ 

የሼክ ሙሀመድ አላሙዲን ከህዝብ እይታ መጥፋት አነጋጋሪ እንደሆነ ነው

ነሀሴ ፲፱ (አስራ ዘጠኝ ) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-የኢህአዴግ ደጋፊ የሆኑት ባለሀብቱ ሼክ ሙሀመድ ሁሴን አልአሙዲን በብጹወ ቅዱስ አቡነ ጳውሎስ የቀብር ስነስርአት እንዲሁም፣ በአቶ መለስ ዜናዊ አስከሬን አቀባባል ዝግጅት ላይ አልተገኙም። አንዳንድ ለኢሳት የደረሱ መረጃዎች እንደሚያሳዩት ባለሀብቱ በሳውዲ ሆስፒታል ህክምና እየተደረገላቸው ነው። ይህንን መረጃ ግን ከነጻ ወገን ማረጋጋጥ አልተቻለም። የባለሀብቱ ኩባንያ የሆነው ሚድሮክ ሰራተኞች በአቶ መለስ ዜና እረፍት ሀዘናቸውን ሲገልጹ የባለሀብቱ ስም አልተጠራም።

የአቶ ሀይለማርያም ጊዜያዊ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ቦታ ኢህአዴግን እያወዛገበ ነው

ነሀሴ ፲፱ (አስራ ዘጠኝ ) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-ከአራት ቀናት በፊት የ ኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊን ሞት ይፋ ባደረገበት ወቅት  ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ እና የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ ፤አቶ መለስን ተክተው በጠቅላይ ሚኒስትርነት እንደሚሰሩ መወሰኑን ይፋ ቢያደርግም፤ በተለይ በህወሀት በኩል በተቀሰቀሰ ከፍተኛ ተቃውሞ እስካሁን  የ አቶ ሀይለማርያም ሹመት ሊጸድቅላቸው እንዳልቻለ  የኢሳት የውስጥ ምንጮች ጠቁመዋል።

አቶ ሀይለማርያም ፤የአቶ መለስ አስከሬን ከብራሰልስ አዲስ አበባ የገባ ዕለት ምሽት  በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽህፈት ቤት ጋዜጣዊ መግለጫ ሢሰጡ፤ “መለስን መተካት ከባድ ነው” ማለታቸው ይታወሳል።

አቶ ሀይለማርያም ይህን ያሉት፤ በእርግጥ ከልባቸው ይሆን?ወይስ የስልጣን ሽኩቻው ሰለባ ላለመሆን ካደረባቸው ስጋት? ወይስ በሌላ አስገዳጅ ተጽዕኖ፤  እስካሁ የታወቀ የለም። ከዚያም በማግስቱ  በዕረፍት ላይ የሚገኘው ፓርላማ አስቸኳይ ስብሰባ መጠራቱ ተነገረ። ስብሰባው የተጠራው የአቶ ሀይለማርያምን የጠቅላይ ሚኒስትርነት ሹመት ለማጽደቅ ነበር። ሆኖም  የስብሰባ ጥሪ በተደረገ በዚያኑ ዕለት ምሽት የኮሙኒኬሽን ጽህፈት ቤት ሚኒስቴር ስብሰባው ላልተወሰነ ጊዜ እንደተላለፈ አስታወቀ። 

Friday 24 August 2012

ሳምሶን ማሞ ክስ በሚኒስተር ዴኤታው ትዕዛዝ ሊቋረጥ ነው


ለሁለት አመት የንግድ ፍቃድ ሳያድሱ በሁለት ድርጅቶች ሲሰሩ ተገኝተው ታስረው በዋስ የወጡት ጋዜጠኛ ሳምሶን ማሞ በፍትህ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ትእዛዝ ክሱ እንዲቋረጥ መደረጉ ተጠቁሟል፡፡

እንደ መረጃ ምንጫችን ታስረው በዋስ ተለቀው ሐሙስ ነሐሴ 17 ቀን 2004. የፌደራሉ ከፍተኛ / ቤት 16 ወንጀል ችሎት የቀረቡት አቶ ሳምሶን ማሞ በጠበቃው አማካኝነት ክሱ መቋረጡን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ምንጮቻችን እንደገለፁት ከሆነ በዕለቱ ዐቃቤ ህግ ምስክሮች እንዲሰማለት ይዞ የቀረበ ሲሆን የሳምሶን ጠበቃ ሚኒስቴር ዴኤታው ክሱ እንዲቋረጥ ደብዳቤ የጻፉ ስለሆነ ጊዜ ሳይባክን ክሱ ይዘጋልን ሲሉ ጠይቀዋል፡፡

ዐቃቢ ህግ በበኩሉ በእርግጥ ደብዳቤው ለእኛም የደረሰን ቢሆንም ምስክርነቱ ተሰምቶ ይቋረጥ ሲል ፍቤቱን ጠይቋል፡፡ በመቀጠልም ምስክርነቱ ከሚሰማ ይቀጠርና እንነጋገርበት የሚል ሀሳብ በማቅረባቸው በጉዳዩ /ቤቱም ደብዳቤው በግልጽ የተጻፈ ስለሆነ ምስክርነቱን መስማቱ ጊዜ ማባከን ነው ካለ በኋላ በመዝገቡ ላይ ውሳኔ ለመስጠት ለሌላ ጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡ በርካታ ዜጎች የንግድ ፈቃድ ባለማደስ እየተከሰሱ በታሰሩበትና በተቀጡበት አገር ለሳምሶን ማሞ ፍትህ ሚኒሰቴር ክሱ እንዲቋረጥ ደብዳቤ መፃፉ አነጋጋሪ ሆኗል፡፡

ከጠ/ሚ መለስ ሞት ጋር በተያያዘ የአንድነት አባላት እየታሰሩ ነው


ከአቶ መለስ ሞት ጋር በተያያዘ በደቡብ ክልላዊ መንግስት ደራሼ ወረዳና በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ቦረና ዞን ቡሌ ሆራ ወረዳ የአንድነት ፓርቲ አባላት እየታሰሩ መሆናቸውን የወረዳው የአንድነት ፓርቲ ሰብሳቢ በተለይ ለፍኖተ ነጻነት ጋዜጣ አስታወቁ፡፡ የወረዳው ሰብሳቢ ለዝግጅት ክፍላችን እንዳስታወቁት ‹‹አቶ መለስ በመሞታቸው ህዝብ ኢህአዴግን በማውገዝና በመቃወም ይንቀሳቀሳል የሚል ስጋት ፈጥሮባቸዋል፡፡
 
ህዝብ ለዚህ አላማ እንዳይንቀሳቀስ በየአካባቢው በህዝብ ተደማጭነት ያላቸውና በወቅቱ ንቁ የፖለቲካ ተሳትፎ ያላቸውን በማደን የፈጠራ ወንጀል በመፈብረክ እየታሰሩ ናቸው፡፡ ›› ይላሉ፡ የደራሼ ወረዳ አንድነት ፓርቲ ሰብሳቢ የሆኑት አቶ ዳፊኮ ታዬ ለዝግጅት ክፍላችን እንደገለጹት ‹‹ የአካባቢው የኢህአዴግ ካድሬዎችና ደህንነቶች ተሰባስበው በህዝብ መካከል መለስ ታሟል መለስ ሞቷል እያሉ የሚያወሩትን እየተከታተሉ ለማሰር ማቀዳቸውን መረጃ ደረሰን፡፡ እኛም በበኩላችን ለአባሎቻችንና ለደጋፊዎቻችን ይህንኑ አስታወቅን፡፡ በመረጃ ባልተደገፈ ወሬ ላይ እዳይሳተፉ አደረግን፡፡ የአቶ መለስ ሞት ይፋ እስከተደረገበት እለት ድረስ ታደለ ተመስጌን፣ ግርማ ዓለሙ፣ ገናናው፣ ገነትና ስጦታው ግርማ የተባሉ የፓርቲው አባላት ‹‹መለስ ሞቷል ብላችኋል›› ተብለው ታሰሩ፡፡ መሞታቸው በመንግስት ከተገለፀ በኋላ ክሱን ቀይረው ህዝብን ለአመጽ ቀስቅሳችኋል በሚል ቀየሩት፡፡

እነሆ በድብርት ስሜት ተፃፈ፤ “ተሜም እንደዋዛ!” .....ከአቤ ቶክቻው

ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ መሞታቸውን “ታማኙ” ኢቲቪ ነገሮናል። በርካቶችን “መርዶ ነጋሪ አትሁኑ” እያለ የሚሰብከው መንግስታችን የጠቅላዩን መሞት የስራ ባህሪው ስላልሆነ አይነግረንም ብለን ብናስብም ከባህሉ ባፈነገጠ መልኩ መርዶ ነገሮናል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ መታመማቸውን እና ሳይሞቱ እንደማይቀር ጭምጭምታ መስማቱን የዘገበው ተመስገን ደሳለኝ ግን፤ “ምን ሲደረግ ታመሙ ትላለህ እንዴት ሆኖ ታሟርትባቸዋለህ…?” ተብሎ ሰላሳ ሺህ የታተሙ ጋዜጣዎቹ  በብላሽ እንዲቃጠሉ እንዲሁም ከዛች ጊዜ በኋላም ተወዳጇ ፍትህ ጋዜጣ ከነጭርሹ እንዳትታተም በመቀጠልም እርሱም ወደ እስር ቤት እንዲሄድ ተደረገ።

እስከ ትላንት ድረስ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የጠቅላይ ሚኒስትሩን ሞት እና የሀዘን እንጉርጉሮ ስመለከት ጠቅላዩ ያደረጉትን ሁሉ እረስቼው በሀዘን ውስጥ ሰጥሜ አንዳንዴም ማለቀስ ሲያሰኘኝ ነበር። ድንገት ትላንት ወዳጄ ተሜ መታሰሩን ስሰማ ሀገሪቷን ወደ እስር ቤት እንዴት እንደለወጧት ድጋሚ ትዝ አለኝ። ድጋሚ እንደርሳቸው ያላሰበ በሙሉን “አሸባሪ” ሲሉ የነበረው ፈሊጣቸው ታወሰኝ። ድጋሚ “ጣቱን የቀሰረ ጣቱ ይቆረጣል” ብለው ሲያሰፈራሩን ታዩኝ።

ሙት አይወቀስም በሚለው ሀገራዊ ብሂል መሰረት በተሜ እስር ሳቢያ ትዝ ያሉኝን በደሎች ለጊዜው ከመዘርዘር እቆጠባለሁ። ቢያንስ ቀብር እስኪያልፍ በአደባባይ እንዲህ በደለው እንዲህ አድርገው ብለን ብንወቅሳቸው መልካም አይደለም።

ጋዜጠኞችንና የፖለቲካ እስረኞችን ለማሰፈታት ሸምግልና እየተካሄደ ነው

ነሀሴ ፲፯ (አስራ ሰባት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በፕሮፌሰር ኤፍሬም ይስሐቅ የሚመራው ራሱን “የኢትዮጽያ የሸማግሌዎች ኀብረት” በሚል የሚጠራው ቡድን ትላንት ነሐሴ 16 ቀን 2004 ዓ.ም፣  ማምሻውን በሸራተን ሆቴል በሰጠው መግለጫ “ሰላም ወዳድ ነበሩ” ያላቸውን በአቶ መለስ ዜናዊ ፤ዜና ዕረፍት የተሰማውን ሐዘን በገለጸበት መግለጫው በመጪው መስከረም ወር በዓልን አስታኮ ለእስረኞች ምህረት ለማድረግ ጠ/ሚኒስትሩ ቃል ገብተው ነበር ሲል ተናገረ።

ፕሮፌሰር ኤፍሬም አሁን በእስር ላይ ባሉት ወገኖች ጉዳይ ጠ/ሚኒስትሩን አነጋግረው “በመስከረም ኑ፣አዲስ ዓመትን ተመርኩዘን ብዙ ችግሮችን እንፈታለን” የሚል ቃል እንደገቡላቸው አስታውሰው፣ተተኪው ጠ/ሚኒስትርም ይህንኑ አክብረው ተግባራዊ እንደሚያደርጉ እንደማይጠራጠሩ ገልጸዋል፡፡

የኮሚቴው አባል የሆኑትና በቅርቡ የዕርቅ ሰነድ ፈርመው ወደአገር ቤት ከገቡት መካከል አንዱ የሆኑት አቶ አባቢያ አባጆቤ አባዱላ በበኩላቸው ቡድኑ የፖለቲካ እስረኞች እንዲፈቱ ጥረት ሲያደርጉ መቆየታቸውን፣በጠ/ሚኒስትሩ በኩልም እስር ቤቶችን ባዶ አደርግላችሃለሁ እስከማለት ቃል እንደተገባላቸው አስታውሰዋል፡፡

የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ የቀብር ስነ ስርዓት በቅድስት ስላሴ ካቴድራል ተፈፀመ

ነሀሴ ፲፯ (አስራ ሰባት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በኢትዮጵያ የፕትርክና ታሪክ አወዛጋቢ የሆኑት ብጹወ ቅዱስ አቡነ ጳውሎስ የመንግስት ባለስልጣናት እና ሌሎች ዲፐሎማቶች በተገኙበት ዛሬ በቅድስት ስላሴ ቤተክርስቲያን የቀብራቸው ስነስርአት ተፈጽሟል።

ከሃምሌ 5 ቀን 2004 ዓ.ም ጀምሮ 20ኛ አመት በአለ ሲመታቸውን ሲያከብሩ የነበሩት አቡነ ጳውሎስ፣ በድንገት ማረፋቸው የብዙዎች መነጋገሪያ አጀንዳ እንደሆነ ነው። በተለይም የእርሳቸውን ሞት ተከትሎ የአቶ መለስ ዜናዊ ዜና እረፍት ይፋ መሆን ኢትዮጵያውያን ነገሩን ከሀይማኖት ጋር እንዲያያዙት ግድ ብሎአቸዋል።

አቡነ ጳውሎስ በልማቱ ዙሪያና ኤች አይ ቪ ኤድስን በመከላከል ረገድ አወንታዊ ተግባራትን መፈጸማቸው ቢነገርም፣ ጥንታዊቷን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንን ከሁለት በመክፈልና በማዳከም፣ የገዢው ፓርቲ መሳሪያ በመሆን እና ከህዝብ ጎን ባለመቆም እንዲሁም ለአለማዊ ቅንጦት ከፍተኛ ቦታ በመስጠታቸው ይወቀሳሉ። በተለይም በቅርቡ የብጹአን አባቶች መደብደብ እና ሀውልታቸውን በቁማቸው ማሰራታቸው ለከፍተኛ ትችት ዳርጓቸው እንደነበር ይታወሳል።

አቶ በረከት ስምኦን ባለስልጣኖች አቶ መለስ ዜናዊን አርዓያ በማድረግ ተከትለው እንዲሄዱ ተማጸኑ

ነሀሴ ፲፯ (አስራ ሰባት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም

ኢሳት ዜና:-አቶ በረከት ዛሬ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ “በሀይወት ዘመናቸው አቶ መለስ የያዙት  ዓላማ የጥቂቶች ዓላማ ከሆነ ሞት ነበር ” ብለዋል ።

የመንግስትና የኢህአዴግ አመራርም የህዝቡን መልዕክት ተቀብለን ጠቅላይ ሚኒስትሩን አርዓያ አደርገን ለመከተል ወስነናል የሚሉት አቶ በረከት፤ ሌሎች ባለስልጣኖችና የኢህአዴግ አመራር አካላት፣ ህዝቡ እና የአለማቀፉ ማህበረሰብ ከጎናቸው እንዲቆም ተማጽነዋል።

ኢሳት በትንናት ዘገባው አንድ የብአዴን ከፍተኛ ባለስልጣንን በምንጭነት በመጠቀም ፣ የኢህአዴግ ባለስልጣናት በአቶ መለስ ሞት የህዝብ ድጋፍ ለማግኘት ስትራቴጂ መንደፉቸውን መግለጻችን ይታወሳል። የኢህአዴግ   ስልት ህዝቡ በየወረዳዎች በተዘረጋው ድንኳን እየወጣ ለአቶ መለስና ለኢህአዴግ ያለውን ድጋፍ እንዲገልጽና ስሜታቸው የተዳከመውን የመንግስት ባለስልጣናት እና የኢህአዴግ ካድሬዎችን እንዲያበረታታ ማድረግ ነው።

አቶ በረከት “በ መለስ አጥንት” በማለት ዛሬ ለባለስልጣኖቹና ለህዝቡ ያቀረቡት ጥሪ በኢህአዴግ ውስጥ የተፈጠረውን መከፋፈል እና ውጥረት እንደሚያሳይ ነው ታዛቢዎች የሚናገሩት።

Thursday 23 August 2012

ተወዳጁ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ቃሊቲ እስር ቤት ተወሰደ!





የፍትህ ጋዜጣ አዘጋጅ ተመስገን ደሳለኝ ባለፈው ሳምንት ውስጥ ፍርድ ቤት ቀርቦ እንደነበር ይታወቃል። በቀረበበትም እለት በርካታ አድናቂዎቹ እና የፍትህ ጋዜጣ አንባቢ ወዳጆች ፍርድ ቤቱን አጨናነቀውት የነበረ ቢሆንም ዳኛ አልተሟላም በሚል ሰበብ ለዛሬ ነሐሴ 16/2004 ዓ.ም  ተቀጥሮ ነበር።

በዛሬው እለት የተመስገንን ክስ የተመለከተው ፍርድ ቤቱ ጋዜጠኛው የተከሰሰበት ወንጀል ዋስትና አያሰጥም በሚል ወደ ወደ ቃሊቲ እስር ቤት እንዲወሰድ እና በቀጣይ ነሀሴ 28/ 2004 ዓ.ም እንዲቀርብ ቀጠሮ ሰጥቷል።

አቃቤ ህግ “ፍትህ ጋዜጣ ትታገድልኝ” ሲል ኮሚክ የሆነ ጥያቄ ፍርድ ቤቱን የጠየቀ ሲሆን፤ ጋዜጣዋ ከአንድ ወር በፊት የጠቅላይ ሚኒስትሩን በጠና መታመም ብሎም “ሞተዋል” የሚለውን ጭምጭምታ ከተለያዩ ምንጮች ጠቅሳ ልታትም ስትል ተገኝታለች በሚል መታገዷ ከዛ በኋላም  ታትማ እንደማታውቅ አቃቤ ህግም ተመስገንም ዳኛውም እኛም እናውቃለን!
በመጨረሻም አስተያየት ተመስገን ደሳለኝ በፍትህ ጋዜጣ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ መታመማቸውን እና ሞቱ የሚባል ጭምጭምታም እንዳለ ሲዘግብ ወደ ቃሊቲ እስር ቤት ተወሰደ። ጋዜጣውም ታገደ። ታድያ፤ ከትላንት ወዲያ በጠዋቱ የጠቅላይ ሚኒስትሩን መሞት መርዶ ነግሮን እስከ አሁንም ድረስ በዋሽንት እንጉርጉሮ እንባ የሚያራጨን ኢቲቪስ ማነው የሚያስረው!?
ኧረ የፍትህ ያለ!  ብንል የሚሰማን ይኖር ይሆን!?