Welcome

"The thing that lies at the foundation of positive change, the way I see it, is service to a fellow human being." - Lech Walesa

Sunday 28 July 2013

‹‹የቢሮ ፖለቲካ ስለበቃን ወደ ሕዝቡ ሄደን ማስተማርና መቀስቀስ አለብን›› አቶ አስራት ጣሴ፣ የአንድነት ፓርቲ ዋና ጸሐፊ

‹‹የቢሮ ፖለቲካ ስለበቃን ወደ ሕዝቡ ሄደን ማስተማርና መቀስቀስ አለብን›› አቶ አስራት ጣሴ፣ የአንድነት ፓርቲ ዋና ጸሐፊሰሞኑን በኢትዮጵያ ተቃውሞ ፖለቲካ ጎራ ብዙም ባልተለመደ ሁኔታ የምርጫ ወቅት ከመድረሱ ‹‹እጅግ›› ቀደም ብሎ ሕዝባዊ ስብሰባና ሠልፍ እዚህም እዚያም እየተካሄደ ይገኛል፡፡ በቀጣይነትም በተለያዩ ፖለቲካዊ አጀንዳዎች ጥላ ሥር በርካታ ሠልፎችንና ሕዝባዊ ስብሰባዎችን ለመጥራት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑ ታውቋል፡፡
ባለፉት ሳምንታት ሕዝባዊ ሠልፎችንና ስብሰባዎችን ካካሄዱ ተቃዋሚ ድርጅቶች መካከል በቅርቡ የተመሠረተው ሰማያዊ ፓርቲ፣ በተቃውሞ ፖለቲካ ውስጥ የጎላ ተሳትፎ ያለው አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትሕ (አንድነት) ፓርቲና የስድስት ፓርቲዎች ግንባር የሆነው የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) ናቸው፡፡ እነዚህ የፖለቲካ ድርጅቶች በአዲስ አበባ፣ በመቀሌ፣ በጎንደርና በደሴ ከተሞች ሕዝባዊ ሠልፎችንና የተቃውሞ ስብሰባዎች አካሂደዋል፡፡ እነዚህ ድርጅቶች በቀጣይነትም በተለያዩ ቦታዎች የተቃውሞ አንቅስቃሴዎችን ለማካሄድ እየተዘጋጁ መሆኑ ታውቋል፡፡ ይህንን ወቅታዊ ጉዳይ በተመለከተ የመድረክ ሥራ አስፈጻሚ አባልና የአንድነት ፓርቲ ዋና ጸሐፊ አቶ አስራት ጣሴን ውድነህ ዘነበ አነጋግሯቸዋል፡፡ አቶ አስራት በኢትዮጵያ የተቃውሞ ፖለቲካ ዙርያ የነቃ ተሳትፎ ከሚያደርጉ ግለሰቦች መካከል ተጠቃሽ ናቸው፡፡ 


ሪፖርተር፡- ሰሞኑን የእርስዎ ፓርቲ በጎንደርና በደሴ የተቃውሞ ትዕይንተ ሕዝብ አካሂዷል፡፡ ፓርቲው ለሕዝቡ ምን ማሳየትና ምን ማድረግ ፈልጐ ነው ትዕይንቱን ያካሄደው?



አቶ አስራት፡- ለዚህ ጥያቄ መልስ ለመስጠት ትንሽ ወደኋላ መለስ ማለት ያስፈልጋል፡፡ ከ2002 ምርጫ በኋላ አንድነትም እንደ አንድነት፣ ሌሎቹም ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ቢሆኑ ሕዝብ ውስጥ ገብተው የማንቃት ሥራና ሕዝባዊ እንቅስቃሴ የመፍጠር ሥራ በተገቢው አልሠሩም፡፡ በጭራሽ በተገቢው መንገድ አልተሠራም፡፡ እርግጥ ሁልጊዜ ማማኸኛ አለን፡፡ ጥርጥር የለውም አዳራሽ ማግኘት አይቻልም፡፡ ሰላማዊ ሠልፍ መውጣትም አይቻልም፡፡ ብዙ ጊዜ አዳራሽ እየተከራየን ገንዘባችሁን መልሳችሁ ውሰዱ እየተባልን ተቸግረን ነበር፡፡ በሌላ በኩልም ስናየው ፍኖተ ነፃነት ጋዜጣ ለአንድነት ፓርቲ ትልቁ መሣርያ ነበር፡፡ ሕዝብን ለማደራጀትና ለማንቃት፤ እንደገና ከሕዝቡም የሚመጡ ሐሳቦችን የምናገኝበት ነበር፡፡ በተለያዩ ስልቶች ጋዜጣው ከሕትመት እንዲወጣ ተደረገ፡፡ መጀመርያ ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት እንዳያትም ተደረገ፡፡ ጋዜጣው እንዳይታተም ለተደረገበት የሚሰጡ ምክንያቶች ሁሉ በቀልድና ሹፈት ደረጃ የሚታዩ ናቸው፡፡   


በግል ማተሚያ ቤቶችም አንድ ጊዜ ያትሙልንና በድጋሚ ልናሳትም ስንሄድ ‹‹እባካችሁ ልጆቻችንን እናሳድግ›› ይሉናል፡፡ ቀብድ ወስደውም የማያትሙና ገንዘቡን አሻፈረኝ ብለው የሚመልሱ አሉ፡፡ 


ይህንን ያነሳሁት ሕዝብን ለማንቀሳቀስ ዕድሎቹ በጣም ጠበቡ ለማለት ነው፡፡ ይህ ውጫዊ ችግራችን ነው፡፡ ነገር ግን ወደዚህ እንቅስቃሴ ከመግባታችን በፊት አንዳንዶቻችን ራሳችን ማፈር ጀምረን ነበር፡፡ እኔ በግሌ ማፈር ከጀመርኩ ቆይቻለሁ፡፡ የፖለቲካ ፓርቲ ሆኖ የፖለቲካ ሥራ መሥራት ወይም መምራት ካልተቻለ አስቸጋሪ ነው፡፡ አንዳንዶቻችን ኢንተርቪው ሰጪዎች ብቻ ሆንን፡፡ ኢንተርቪው ሰጪ የቢሮ ፖለቲከኞች ከሆንን ይህ አካሄድ የፖለቲካ ሥራን አይመጥንም፡፡ ፖለቲካን በቢሮ ውስጥ ሆኖ መሥራት አመራሮቻችንን አይመጥንም፡፡ አጥራችንን ሰብረን መውጣት አለብን፡፡ ሕዝቡ መሀል ገብተን ሕዝባዊ እንቅስቃሴ መፍጠር አለብን፡፡ ያለበለዚያ በአንዳንዶቻችን እምነት በእውነት አስፈላጊዎች አይደለንም፡፡ ምናልባት ረዥም ጊዜ ፖለቲካው ቦታ ላይ ኃላፊነት ይዘን በመቆየታችን፣ በወጣቶች ሊሠራ የሚችለውን ሥራ የዘነጋን ይመስለናል፡፡ ራሳችንን መታዘብ ደረጃ ላይ በመድረሳችን የሆነ ነገር መደረግ አለበት አልን፡፡ አጥራችን መሰበር አለበት፡፡ ሕገ መንግሥታዊ መብታችንን ማስከበር አለብን፡፡ ይህንን መሠረት አድርገን ወደ ሕዝብ እንሂድ ብለን ነው የተነሳነው፡፡ 


ሪፖርተር፡- ሰላማዊ ሠልፎችን ከዚህ ቀደም ማካሄድ የተዘጋ ነው ብለውኛል፡፡ በአሁኑ ወቅት በጎንደርና በደሴ ማካሄድ ችላችኋል፡፡ አሁን መንግሥት ተለሳልሶ ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል ማለት ይቻላል?


አቶ አስራት፡- እኔ ከኢሕአዴግ በኩል ምንም የመለሳለስ ሁኔታ አላየሁም፡፡ የመለሳለስ ሁኔታ አላየሁም ስል በሁለቱም ቦታዎች ያካሄድናቸውንና በአዲስ አበባ ለማካሄድ ያሰብነውን መሠረት በማድረግ ነው፡፡ ደሴ ላይ በጭራሽ ልናደርግ እንዳንችል ተገቢ ባልሆነ መንገድ እንቅፋት ሲፈጥሩ ነበር፡፡ በተለይ በጎንደር እኔ በነበርኩበት ቦታ እገታ ጭምር ነበር፡፡ የእኛ የሥራ አስፈጻሚ አባላት፣ የብሔራዊ ምክር ቤት ሰብሳቢው፣ የብሔራዊ ምክር ቤት አባሎቻችንና መኪኖቻቸው ሳይቀሩ እንዳይንቀሳቀሱ ተደርገው ነበር፡፡ የከተማው ከንቲባና የዞኑ መስተዳድር አናነጋግራችሁም፣ እንዲያውም አልፎ ተርፎ በዚህ ከተማ ምንም ዓይነት ሰላማዊ ሠልፍ አይሞከርም ብለው ነበር፡፡ 


ምክንያታቸውም አካባቢው የፀጥታ ችግር ያለበት ስለሆነ እዚህ የመጣችሁት ግርግር ለመፍጠር ነው የሚል ነው፡፡ በአደባባይ ሰው በሚሰማበት ቦታ ላይ ‹‹እደፋሃለሁ፣ እንደፋችኋለን፤›› እየተባልን ነበር፡፡ እስከ መጨረሻው ድረስ ያነጋገረን ኃይል አልነበረም፡፡ የትኛውም መስዋዕትነት ይከፈል፣ የሚያስከፍለውን ያህል ዋጋ ያስከፍል እንጂ ሰላማዊ ሠልፉን እንወጣለን አልን፡፡ በሕጉ መሠረት መከልከል አይችሉም፡፡ የሚፈለገው ማሳወቅ ነው፡፡ ሠልፍ እንደምናካሂድ አሳውቀናል፡፡ በዚህ መሠረት ተዘጋጅተን ስንጠብቅ ከፖሊስ ውይይት እናድርግ የሚል ጥሪ ቀረበልን፡፡ ከተወያየን በኋላም ብዙ ተፅዕኖ ተደርጎብንም ቢሆን ሠልፉን አድርገናል፡፡       
  
ሪፖርተር፡- ሠልፎቹን ከማካሄዳችሁ በፊት ግምት ይኖራችኋል ብዬ አስባለሁ፡፡ እናንተ ያሰባችሁትን ያህል ሠልፈኛ መጥቶላችኋል? ይህንን የምጠይቅዎ በተፅዕኖም ሆነ በሌላ ምክንያት የወጣው ሕዝብ ቁጥር አነስተኛ ነው የሚሉ ስላሉ ነው፡፡



አቶ አስራት፡- እኛ ቁጥርን በሁለተኛ ደረጃ ነው የምናየው፡፡ አንደኛው መርህ ነው፡፡ የቢሮ ፖለቲካ በቃ፡፡ የቢሮ ፖለቲካ ስለበቃን ወደ ሕዝብ ሄደን ማስተማርና መቀስቀስ አለብን፡፡ ሕዝቡ ለሕገ መንግሥታዊ መብቱ እንዲቆም መቀስቀስ አለብን፡፡ ከገባበት የፍርኃት ቆፈን እንዲወጣ ወደ ሕዝቡ ሄደን ሊከፈል የሚገባውን መስዋዕትነት ከፍለን መሥራት አለብን የሚለው አንዱ ትልቁ ስኬት ወይም ግኝት ነው፡፡ ከስምንት ዓመት በኋላ ነው በጎንደር ሰላማዊ ሠልፍ የተካሄደው፡፡ በሁለተኛ ደረጃ እንዳልከው ብዙ ሕዝብ መጠበቅ አንድ ሰላማዊ ሠልፍ የሚጠራ ክፍል ተግባር ነው፡፡ ብዙ ሕዝብ ባገኘ ቁጥር የፖለቲካ ትርጉሙ ትልቅ ይሆናል፡፡ ነገር ግን በኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ በአሁኑ ጊዜ ለመጀመርያ ጊዜ በሚካሄዱ ሰላማዊ ሠልፎች በእውነት የናረ ቁጥር አዕምሮአችን ውስጥ የለም፡፡ መቼስ የወጣውን ሰው አትቆጥርም፡፡ 


መንግሥትም ታች አውርዶ ይገምታል፡፡ እኛም ትንሽ ከፍ እናደርግ ይሁን አናውቅም በጎንደር ከ20 እስከ 25 ሺሕ ሰው ወጥቷል፡፡ በደሴ ደግሞ እስከ 50 ሺሕ ሰው ወጥቷል፡፡ በአሁኑ ጊዜ ለእኔ ቁጥር ሁለተኛ ደረጃ ነው፤ ወደፊት ግን ቁጥርም አስፈላጊ ነው፡፡ ሕዝቡ በገፍ ወጥቶ ያለውን ችግር በመግለጽ ያለውንም ድጋፍ ለተቃዋሚዎች ካላሳየ አስቸጋሪ ነው፡፡ ችግር አለ ማለት ነው፡፡ እኛ ውጤታማ ነበርን ነው የምንለው፡፡ 
   
ሪፖርተር፡- በሕጉ መሠረት ሰላማዊ ሠልፍ ለማካሄድ ማሳወቅ እንጂ ማስፈቀድ አይጠበቅም፡፡ ቀደም ሲል ሰላማዊ ሠልፍ ለማካሄድ ተከለከልን ትሉ ነበር፡፡ በአሁኑ ወቅት ሰላማዊ ሠልፍ እያካሄዳችሁ ነው፡፡ ምን የተለየ አሠራር መጣ?



አቶ አስራት፡- ጥያቄው ትንሽ ከበድ ይላል፡፡ ከበድ ይላል የምልበት ከምን አንፃር ነው? ቅድም ካነሳሁት አንፃር በእውነት ቀደም ሲልም አሳውቀን መውጣት ነበረብን፡፡ እኛ ዝም ብለን ይህ ነው በማንለው ምክንያት [አልወጣንም]፡፡ አንዱ ፍርኃት መሆን አለበት፡፡ መቼም በ1997 ዓ.ም. የደረሰውን የሕዝብ እልቂት አይተናል፡፡ የሥርዓቱን የመጨረሻ የአምባገነንነት ደረጃም ተመልክተነዋል፡፡ ለሃያ ሁለት ወራት እስር ቤት በነበርንበት ጊዜ ያለምንም ምክንያትና ማስረጃ በዘር ማጥፋት መክሰስ የሚችል ሥርዓት መሆኑን ተረድተናል፡፡ እንደምታውቀው ከጥቅምት 1998 ዓ.ም. ጀምሮ 100 ሺዎች ለእስር ተዳርገው ነበር፡፡ በክፉ ቦታዎች ነበር እስሩ፡፡ በሰውነታቸው ላይ የደረሰ ጉዳት ነበር፡፡ 


ቅንጅትን ደግፎ የተነሳው ክፍልም ተመቷል፡፡ እኛም በእነዚህ ምክንያቶች ረጋ ብለን እንድናስብ ሆነናል፡፡ ያ ጊዜ ተመልሶ ይመጣል የሚል ሥጋት በመኖሩ ረዘም ላለ ጊዜ ማለትም ለአራት ዓመት የአየሩንና የሕዝቡን ሁኔታ ስንለካ ነበር፡፡ አንድ ወቅት ግን መቆም አለበት፡፡ ወይ ፖለቲካውን ፖለቲካ አድርገን እንሥራው ወይ እንተወው፡፡ ካልሠራነው ለሚሠሩ ሰዎች እንተው በሚለው ጉዳይ ደጋግመን ተነጋገርንበት፡፡ ከዚያም ሕገ መንግሥቱንና መብታችንን እናስከብራለን፡፡ መብታችንን ለማስከበር በምናደርገው እንቅስቃሴ የሚደርስብንን ሁሉ እንቀበላለን በሚል ነው ይህ እንቅስቃሴ የተጀመረው፡፡ 
    
ሪፖርተር፡- ብዙ ጊዜ ተቃዋሚዎች ሰላማዊ ሠልፍና ቅስቀሳዎችን የምታካሂዱት ምርጫ በሚደርስበት ወቅት ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ደግሞ አንድነትና ሌሎች የፖለቲካ ፓርቲዎች ምርጫ ከመድረሱ በጣም ቀደም ብላችሁ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ ናችሁ፡፡ ይህንን ልታደርጉ የቻላችሁበት የፖለቲካ ትንታኔ ምንድነው? በፖለቲካ ፓርቲዎች አካባቢ የአካሄድ ለውጥ ሊታይ የቻለበት ምክንያትስ ምንድነው?



አቶ አስራት፡- ያለንበት ሁኔታ ነው፡፡ አገራችን አደገኛ ወቅት ላይ ነው ያለችው፡፡ ጥናቶችን ልጥቀስ፡፡ ‹‹ዘ ኢኮኖሚስት ኢንተለጀንት ዩኒት›› የዲሞክራሲ ደረጃን ለመለየት 60 መመዘኛዎችን ተጠቅሞ አገሮችን በአራት ከፍሏል፡፡ በዚህ መሠረት ሙሉ ዲሞክራሲ፣ እንከን ያለበት ዲሞክራሲ፣ ድቅል አገዛዝ (አንዳንዴ ዲሞክራሲ አንዳንዴ አምባገነን) እና የመጨረሻው የለየላቸው አምባገነን በሚሉ ክፍሎች ከፍሏል፡፡ በዚህ መመዘኛ ኢትዮጵያ የተመደበችው ፍፁም አምባገነኖች ከሚባሉት ውስጥ ነው፡፡ 


ሌላ ጥናት አለ፡፡ ‹‹ፍሪደም ሐውስ›› የሚባል ተቋም የነፃነት ደረጃን በሚመለከት አጥንቷል፡፡ ይህ ጥናት አገሮችን በሦስት ከፍሏል፡፡ ነፃ፣ ከፊል ነፃ፣ ነፃ ያልሆኑ በሚል ከፍሏል፡፡ አሁንም ኢትዮጵያ ነፃ ያልሆኑ በሚሉት ጎራ ውስጥ ነው የተመደበችው፡፡ መመዘኛዎቹ ግልጽ፣ ተዓማኒና ነፃ ምርጫ መካሄዱ፣ ውድድር ያለበት የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት መኖሩ፣ ፖለቲካዊ ፉክክር ያለበት ምርጫ መካሄዱ፣ የምርጫ ሚስጥራዊነት የተጠበቀ መሆኑና የነቃ የሕዝብ ተሳትፎ ያለበት መሆኑ እንደ መስፈርት ተቀምጧል ይላል፡፡ በዚህም ብትመለከት ኢትዮጵያ የተመደበችው ፍፁም ነፃ ያልሆኑ አገሮች ምድብ ውስጥ ነው፡፡ 


ከዚህ ሁሉ የሚያሰጋው ‹‹ፎሬን ፖሊሲ ሜጋዚንና ፈንድ ፎር ፒስ›› የሚባል ድርጅት ባደረገው ጥናት የዓለም አገሮች የሚገኙበትን የመረጋጋት ሁኔታ በተወሰኑ መስፈርቶች አወዳድሮ፣ ኢትዮጵያ ዝቅተኛ ነጥብ በማግኘት የመከነ አገር (ፌልድ ስቴት) ለመሆን ከተቃረቡትና አሳሳቢ ከተባሉት አገሮች ቀጥላ አደጋ ዞን ውስጥ ተመድባለች፡፡ 


እነዚህን ነጥቦች ያነሳሁት ጉዳዩ የሥልጣን ጉዳይ ስለሆነ ብቻ አይደለም፡፡ ጉዳዩ የአገር ህልውናም ጭምር ነው፡፡ ባለንበት ሁኔታ የሙስናውን ሁኔታ ታዩታላችሁ፡፡ እ.ኤ.አ. ከ2000 እስከ 2013 ድረስ 16.5 ቢሊዮን ዶላር ከኢትዮጵያ ወጥቷል፡፡ ገንዘቡ የወጣው በሙስናና በሕገወጥ የገንዘብ ዝውውር አማካይነት ነው፡፡ በህዳሴ ግድብ ዋጋ ተመን ብንመለከተው ሦስት የህዳሴ ግድቦችን ይገነባል፡፡ ሕዝቡ በገፍ ይሰደዳል የኑሮ ውድነቱ ከፍቷል፡፡ ይኼ ጉዳይ አቅጣጫውን ስቶ ከመሄዱ በፊት የምንችለውን ያህል አገር የማዳን ሥራ መሠራት አለበት በማለት ነው የተነሳነው፡፡ እንደ አገርና እንደ ሕዝብ ለመቀጠል ጥያቄ ውስጥ ነው ያለነው፡፡    


ሪፖርተር፡-  የፖለቲካ ድርጅቶች ሁሉ እንቅስቃሴ የጀመራችሁት ይህንን አስባችሁ ነው? ከምርጫ በፊት እንቅስቃሴ ውስጥ የገባችሁት በዚህ መነሻነት ነው ማለት ይቻላል?


አቶ አስራት፡- የአንድነትን በድፍረት መናገር እችላለሁ፡፡ ሌሎችም ቢሆኑ ከዚህ የተለየ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ የአገሪቷን ተጨባጭ ሁኔታ፣ የሰፈነውን አምባገነናዊነት፣ የሰፈነውን የሰብዓዊ መብት ረገጣ፣ የፍርድ ቤቶችን ነፃ ያለመሆንና የሕግ የበላይነት የመሳሰሉት ችግሮች መከበር አለባቸው በሚል ነው፡፡ የፀረ ሽብርተኝነት አዋጁ ሕገ መንግሥቱን ስድስትና ሰባት ቦታ ይጥሳል፡፡ በዚህ ምክንያት ነው የተነሳነው፡፡    


ሪፖርተር፡- ሕዝቡ እነዚህን ጉዳዮች እንዲረዳላችሁ ፈለጋችሁ እንበል፡፡ ከዚያ የሚቀጥለው መንግሥት እነዚህን ነጥቦች እንዲያስተካክል ነው? ወይስ በሥልጣን ጥያቄ ትገፋላችሁ?


አቶ አስራት፡- ግልጽ ነው፡፡ አንደኛ የፀረ ሽብር አዋጅ እንዲሰረዝ ነው የምንጠይቀው፡፡ ሁለተኛ የሕዝቡ ሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ይከበሩ፡፡ መብትህን አስከብር ነው የምንለው፡፡ ሕዝቡ ነፃ ዳኝነት ያግኝ የሕግ የበላይነት ይከበር፡፡ መልካም አስተዳደር ከነጭራሹ የለም፡፡ መልካም አስተዳዳር መስፈን አለበት፡፡ ሙስና የሥርዓቱ መገለጫ ሆኗል፤ መቆም አለበት፡፡ ጥፋተኞች መቀጣት አለባቸው፡፡ መንግሥት በሕዝቡ ውስጥ ተገቢውን መረጋጋትና መግባባት ለመፍጠር አልቻለም፡፡ መንግሥት የሕዝብ አመኔታ ሊያገኝ አልቻለም፡፡ ይህ ሊሆን ይችል ዘንድ ከጉዳዩ ባለቤት፣ ይመለከተናል ከሚሉ ባለድርሻዎች፣ ከፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ከሲቪክ ማኅበራት፣ ከአገር ሽማግሌዎችና ከምሁራን ጋር ቁጭ ብሎ ብሔራዊ መግባቢያና ብሔራዊ የውይይት መድረክ መክፈት አለበት፡፡ ምክንያቱም አሁን ባለው ሁኔታ መንግሥት ሕዝቡንና አገሪቱን እያስተዳደረ አይደለም፡፡ መነጋገርና መወያየት አለበት፡፡


በምንም መንገድ ግን ተቃዋሚ ፓርቲ አንድነትም ሆነ እኔ በቅርብ የማውቀው መድረክም ከመንግሥት በአቋራጭ የሚጠይቁት የሥልጣን ጉዳይ የለም፡፡ ሥልጣን የሚመነጨው ከምርጫ ሳጥን ነው ብለን ነው የምናምነው፡፡ በዚህ ሕዝባዊ እንቅስቃሴ አንዱ ሕዝብ ለመብቱ እንዲቆምና በ2007 ምርጫ ተገቢ ነው ብሎ የሚያስበውን ፓርቲ መርጦ ወደ ሥልጣን እንዲያመጣ፣ ኢትዮጵያ እንደ አገር አቅጣጫዋን እንድትይዝ ነው፡፡     


ሪፖርተር፡- የእርስዎ ፓርቲም ሆነ የታቀፈበት መድረክ በተካሄዱ ምርጫዎች ብዙም ተሳታፊ አይደሉም፡፡ በ2007 ዓ.ም. በሚካሄደው ምርጫ አቋማችሁን አሁን ላይ መናገር ከባድ ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን በምርጫ ንቁ ተሳታፊ ሳትሆኑ እነዚህ ቅስቀሳዎችን እንዴት ልትጠቀሙባቸው አስባችኋል? ከዚህ ጋር ደግሞ ሁለት ጊዜ ያልተወዳደረ ፓርቲ ከጨዋታ ውጭ ይሆናል የሚል የምርጫ ቦርድ ሕግ አለ፡፡


አቶ አስራት፡- ከምርጫ መሰረዝ ከሚለው ልነሳ፡፡ ይኼ የራሴ የግል እምነቴ ነው፡፡ አንድ የፖለቲካ ፓርቲ ነፃ፣ ፍትሐዊና ሚስጥራዊነቱ ባልተጠበቀ ምርጫ ከመሳተፍ ሁለት ጊዜ ሳይወዳደር ቢቀር የተሻለ ነው፡፡ ምክንያቱም ምርጫ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓትን ያሰፍናል፣ የሕግ የበላይነትን ያመጣል፡፡ የምንለው ትልቁ መሣሪያ ካልተስተካከለና ፍትሐዊና ግልጽ ካልሆነ በስተቀር በአገራችን እየተዳደርን ያለነው በ2002 ዓ.ም. በተካሄደው የውሸት ምርጫ ነው፡፡ በውሸት ምርጫ መሳተፍ የሕዝብን ብሶትና መከራ ለማራዘም መተባበር ነው፡፡ ስለዚህ ያ ሊያሳስበን አይገባም፡፡ 


በአዲስ አበባ የአካባቢ ምርጫ ያልተሳተፍንባቸው ምክንያቶች ግልጽ ናቸው፡፡ 18 ጥያቄዎችን ለምርጫ ቦርድና ለጠቅላይ ሚኒስትሩ አቅርበናል፡፡ ሊያወያዩንና ሊያነጋግሩን አልፈለጉም፡፡ 99.6 በመቶ [አሸንፈናል] ያሉትን ልንደግመው አንፈልግም፡፡    


ሪፖርተር፡- በርካታ አገሮች የፀረ ሽብር ሕጎች አሏቸው፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥትም እንደሌሎች አገሮች የፀረ ሽብር ሕግ አውጥቷል፡፡ አንድነት የፀረ ሽብር ሕጉ ይሰረዝ ሲል አማራጭ አቅርቦ ነው? ሌላ ዓይነት አማራጭ ይጠቀማል? ወይስ ከነጭራሹ አያስፈልግም ነው የሚለው?


አቶ አስራት፡- በመሠረቱ በምናውቀው የኢትዮጵያ ታሪክና ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ኢትዮጵያ ለሽብር ተጋላጭ አይደለችም፡፡ በአገራችን ሽብር የሚፈጥሩ አሉ ብለን አናምንም፡፡ ሽብር ቀልድ አይደለም፡፡ ሽብርን የምናውቀው በአፍጋኒስታን ታሊባን የሚያካሂደውን ሽብር ነው፡፡ የነአልቃይዳ ትልቅ ሽብር ነው፡፡ የሶማሊያ አልሸባብ ትልቅ ሽብር ነው፡፡ የናይጀሪያው ቦኮሐራም ትልቅ ሽብር ነው፡፡ ኢትዮጵያ ለእንደዚህ ዓይነት ሽብር የተጋለጠች አገር አይደለችም፡፡ መልክዓ ምድራዊ አቀማመጧ አሳሳቢ ቢሆንም፣ በተጨባጭ ግን ይህ የሽብር አዋጅ በወጣበት ጊዜ ኢትዮጵያ እንደዚህ ዓይነት የሽብር ሥጋት አልነበረባትም፡፡ 


ይህ የፀረ ሽብር አዋጅ የወጣው ኢትዮጵያ ለሽብር ተጋልጣ ሳይሆን ተቃዋሚ ፓርቲዎችን፣ በነፃ ፕሬስ ላይ የተሰማሩትንና በሲቪክ ማኅበራት የተሰማሩትን ለማፈን ነው፡፡ በእኛ በኩል ኢትዮጵያን ለሽብር የሚያጋልጡ ሁኔታዎች ሲፈጠሩ ተመጣጣኝ የሆነ ሕግ፣ ተመጣጣኝ የሆነ አዋጅ እንዲኖር እናደርጋለን፡፡ ነገር ግን መኪና በሌለበት አገር የትራፊክ ሕግ ለማውጣት የመሞከር ዓይነት ነው መንግሥት እያደረገ ያለው፡፡ በዚህ ፀረ ሽብር ሕግ ሌላው መታየት ያለበት ኢትዮጵያ ውስጥ ለጥፋት ወይም ለወንጀል የሚሰማሩ ካሉ የኢትዮጵያ ሕግ ይዳኛቸዋል፡፡ ይህ እኮ በቀጥታ መብትን መንፈግ ነው፡፡ ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ እኮ ነው ሕጉ ሊያስር፣ ቤት ሊበረብርና ደም መውሰድ የሚችለው፡፡   


ሪፖርተር፡- ኢትዮጵያ ውስጥ በተለያዩ አካባቢዎችና ጊዜያት የቦምብ ፍንዳታዎች ተከስተው የሰው ሕይወት እንደጠፋ ይታወቃል፡፡ አደጋ ከመድረሱ በፊትም ከነጦር መሣርያዎቻቸው የተያዙ አሉ፡፡ የፀረ ሽብር ሕጉ እንዲወጣ ካደረጉት ምክንያቶች መካከል እነዚህ ተጠቃሽ መሆናቸውን መንግሥት ገልጿል፡፡ እነዚህን በተመለከተ የእናንተ ሐሳብ ምንድነው?


አቶ አስራት፡- እንደ ግለሰብ በእነዚህ ክስተቶች የአሸባሪነት ባህሪ እየመጣ ነው የሚል ሥጋት ለመፍጠር ተፈልጎ እንጂ፣ ለአንዱም ጉዳይ በትክክል የምናገኘው መረጃ የለም፡፡ እስከ መጨረሻ ወጥቶ ለምሳሌ ለፕሬስ በትክክል እነዚህ ሰዎች ማናቸው? ምን አደረጉ? የሚባለው ነገር ተመርምሮ አልቀረበም፡፡ ሕዝብ እኮ መረጃው ቀርቦለት እውነትም አላለም፡፡ እንዲሁ ትንሽ ችግር በመፍጠር ወቅቱን እየተከተሉ ተቃዋሚዎችን ወይም ሊያጠቁ የሚፈልጉትን ክፍል ለማጥቂያ የሚደረግ አካሄድ ነው ብዬ ነው የማየው፡፡ በአገርና በሕዝብ ላይ ትልቅ ሥጋት መጥቶ ነበር የሚል እምነት የለኝም፡፡  
  
ሪፖርተር፡- አንድነትና ዓረና የመድረክ አባል ድርጅቶች እንደሆኑ ይታወቃል፡፡ አንድነትና ዓረና ከመድረክ ውጭ ራሳቸውን ችለው ቅስቀሳ ማካሄዳቸው ታይቷል፡፡ በተለይ አንድነት ከመድረክ ጋር በቅርቡ በጀመረው እሰጥ እገባ ይሆን ለብቻው ቅስቀሳውን ያካሄደው?



አቶ አስራት፡- አንድ መረጃ ላስተካክልልህ፡፡ መቀሌ የተካሄደው ሕዝባዊ ስብሰባ በመድረክ አማካይነት ነው፡፡ እኛም [አንድነት] ትግራይ ቤዝ አለን፡፡ ዓረናም ትግራይ ቤዝ አለው፡፡ በአብዛኛው በዚያ አካባቢ ንቁ ተሳትፎ የሚያደርገው ዓረና በመሆኑ የዓረና መስሎ ነው እንጂ ስብሰባው በመድረክ ስም የተካሄደ ነው፡፡ 


ሌላው እውነት ነው በመድረክና በአንድነት መካከል የተወሰኑ አለመግባባቶች ተፈጥረዋል፡፡ ለእነዚያ አለመግባባቶች መንስዔ የነበረው አንድነት ስትራቴጂካዊ ፕላኑ በሚመራው አቅጣጫ መሠረት ከመድረክ ጋር ያለውን ግንኙነት እንዲገመገም ግምገማው ተካሄደ፡፡ የግምገማውን ውጤት ለመድረክ ሰጠን፡፡ በወቅቱ ቴክኒካዊ የሆነ አንድ ችግር ተፈጠረ፡፡ በወቅቱ የግምገማው ውጤት መድረክ ዘንድ ሳይደርስ ሾልኮ ጋዜጣ ላይ ወጣ፡፡ ቅሬታው የተፈጠረው እዚያ ላይ ነው፡፡ የሚያጣላን የጥናቱ ፍሬ ነገር አይደለም፡፡ የግምገማው ዓላማ መድረክ ካለበት የቆመ የፖለቲካ ሁኔታ ተነስቶ መንቀሳቀስ ካለበት ምን እናድርግ የሚለውን ለማመላከት ነው፡፡ 


መድረክ ሲባል አንድነትንም ይጨምራል፡፡ የፖለቲካ ሥራ መሥራት ባለመቻላችን ሕዝቡን ልናንቀሳቅስ አልቻልንም እንፈትሸው ተባለ፡፡ መድረክ ካለበት እንዲያኮበኩብ ለማድረግ ነው፡፡ እኔም የአጥኝው ቡድን አባል ስለነበርኩ አውቀዋለሁ፡፡ ግን መጀመሪያ በጋዜጣ ከመውጣቱ በፊት ለመድረክ መድረስ ነበረበት፤ ቀጥሎም መምከር ነበረብን በሚል ነው፡፡


ይኼ ማለት ግን አካሄዱ ችግር ነበረበት ማለት እንጂ የግምገማው ፍሬ ነገር ልክ አይደለም ማለት አይደለም፡፡ በዚህ ነው እንግዲህ መሻከር የመጣው፡፡ በአሁኑ ወቅት ግን እያረገብነው ነው፡፡ ነገር ግን በተወሰኑ ሰዎች ብቻ ችግሮች አይረግቡም፡፡ ያልሆነ ሚና ወስደው የሚጫወቱም አሉ፡፡ ያ አንዳንዴ ችግሩን ያሰፋዋል፡፡ በዚህ በኩልም ጋዜጦችም ጉዳዩ እንዳይበርድ ትፈልጋላችሁ፡፡ ኢሕአዴግም ይፈልጋል፡፡    
  
ሪፖርተር፡- ስለዚህ ችግራችሁን ስላልፈታችሁ ነው እናንተ ከመድረክ ተለይታችሁ የፖለቲካ ቅስቀሳ የጀመራችሁት?



አቶ አስራት፡- ፕሮግራምና ደንብ አለን፡፡ በደንባችን መሠረት የፓርቲው ነፃነት አለ፡፡ ውህደት አልፈጸምንም፡፡ መድረክ ግንባር ነው፡፡ እንደ ግንባርነቱም መድረክ በጋራ ካቀደው ሰላማዊ ሠልፍም ሆነ ስብሰባ ውጭ ፓርቲዎች ሊያካሂዱ ይችላሉ፡፡ በጋራ ያቀድናቸውን በጋራ እናካሂዳለን፡፡ መድረክ አቅሙ ውስን ነው፡፡ አንድነት ደግሞ በራሱ የተሻለ የፋይናንስ አቅም አለው፡፡ ከአባላት መዋጮና ከውጭም ድጋፍ አለው፡፡ [መድረክ] በዚያው ፍጥነት መሄድ አልቻለም፤ አልፈለገምም፡፡   
ሪፖርተር፡- የፖለቲካ ቅስቀሳችሁን የጀመራችሁት በክልል ከተሞች ነው፡፡ ብዙ ጊዜ አዲስ አበባ ላይ ነበር የዚህ ዓይነቱን ሥራ ስትሠሩ የምትስተዋሉት፡፡ የስትራቴጂ ለውጥ አለ? ማግኘት የፈለጋችሁት ውጤትስ ምንድነው?



አቶ አስራት፡- ግብረ ኃይሉ የተሻለ ይመልሰው ነበር፡፡ ግብረ ኃይሉ ይህን ሲያቅድ ፈትሾ ገምግሞ ነው ብዬ ነው የማስበው፡፡ ነገር ግን ጎንደርና ደሴ በተደጋጋሚ ጥያቄ በማቅረባቸው ነው፡፡ ከተሞቹ በተደጋጋሚ ጠይቀዋል፡፡ በዚህ ምክንያት ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ 


አዲስ አበባ ላይ ለማካሄድ እየሞከርን ነው፡፡ ካነሳህልኝ ያለንበትን ችግር ልግለጽልህ፡፡ ባለፈው በራሪ ወረቀቶችንና ማስታወቂያዎችን ለማሠራጨት ከፍተኛ እንቅስቃሴ አድርገናል፡፡ እንቅስቃሴ ውስጥ ስንገባ ቀጥታ ወደ ሰላማዊ ሠልፉ ለመግባት ነበር፡፡ ነገር ግን በጭራሽ ሊያላውሱን አልቻሉም፡፡ በሁለት ቀናት ውስጥ 42 አባሎቻችን ተያዙብን፡፡ ሲያዙ በራሪ ወረቀት በተናችሁ ነው የተባሉት፡፡ በራሪ ወረቀቱ ለሚቀጥለው ሰላማዊ ሠልፍ ሕዝባዊ ስብሰባ ለመጥራት መንደርደሪያ መንገዳችን ነው፡፡


 ፈርሜ የላኩትን አዳራሽ ለማግኘት የሚጠይቁ ደብዳቤዎችን ብዛት ብታይ ታዝናለህ፡፡ ከ30 በላይ ናቸው፡፡ የተሻሻለው የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ አዋጅ ቁጥር 573/2000 አንቀጽ 46 ለፓርቲዎች የዕለት ተዕለት ተግባር ማከናወኛ የሚሰጥ ድጋፍ ስለሚመራበት አሠራር ይደነግጋል፡፡ የፖለቲካ ፓርቲ የሚሰጠውን ድጋፍ ለተመደበለት ተግባር ብቻ ማዋል አለበት ይላል፡፡ የፖለቲካ ፓርቲ የዕለት ተዕለት ተግባር የሚከተሉትን ያካትታል፡፡ አንዱ የሕዝቡን የፖለቲካ ግንዛቤ ማዳበር፤ የፓርቲውን ዓላማ ለሕዝብ ማስረፅ፡፡ ዜጎች በአገሪቱ ፖለቲካ ውስጥ ንቁ ተሳትፎ እንዲኖራቸው መቀስቀስን ያካትታል፡፡ 


ይህ በራሪ ወረቀት የሚሠራው ይኼንን ነው፡፡ 42 አባላቶቻችን የተያዙት ፈቃድ የላችሁም ተብሎ ነው፡፡ ስለዚህ የፖለቲካ ሥራ ማከናወን እንዳንችል የሚያደርገን አየር እየፈጠሩ ነው፡፡ ከሚመለከተው የመንግሥት አካል ጋር በጉዳዩ ላይ ለመነጋገር ጥያቄ አቅርበን በተደጋጋሚ በራቸውን አንኳኳን እስካሁን ምላሽ የለም፡፡     

No comments:

Post a Comment