Welcome

"The thing that lies at the foundation of positive change, the way I see it, is service to a fellow human being." - Lech Walesa

Sunday 7 October 2012

አቶ ጁነዲን ሳዶ ከኦሕዴድ ሥራ አስፈጻሚነት ተወገዱ

በታምሩ ጽጌ
የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትሩ አቶ ጁነዲን ሳዶ ከኦሮሞ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦሕዴድ) ሥራ አስፈጻሚነት ተነስተው በተራ አባልነት እንዲቀጥሉ ድርጅቱ መወሰኑን ምንጮች ለሪፖርተር አስታወቁ፡፡
የኦሕዴድ ሥራ አስፈጻሚ ከመስከረም 21 ቀን እስከ መስከረም 24 ቀን 2005 ዓ.ም. ባካሄደው ዓመታዊ ጉባዔው ላይ፣ በሟች እናታቸው መኖሪያ ላይ እያሠሩት ካለው መስጅድ ጋር በተያያዘ የተገመገሙት ሚኒስትር ጁነዲን፣ ከፍተኛ የዲሲፕሊን ጉድለት መፈጸማቸውንና ካሉበት ኃላፊነትና ሥልጣን አኳያ ተገቢ ያልሆነ ሥራ መሥራታቸው በዋናነት እንደተገመገሙበት ምንጮቹ አረጋግጠዋል፡፡

አቶ ጁነዲን በእናታቸው የኑዛዜ ቃል መሠረት በመኖሪያ ቤታቸው ላይ መስጅድ ለማስገንባት፣ በሚኒስትርነታቸው ሳይሆን በግለሰብ ደረጃ ለመስጅዱ ማስጨረሻ ከሳዑዲ ዓረቢያ ኤምባሲ ዕርዳታ በመጠየቃቸው፣ የመስጅዱ የመጀመሪያ ደረጃ ምርቃት ሲደረግ በኢትዮጵያ የሳዑዲ ዓረቢያ አምባሳደር ተገኝተው 500 ቅዱስ ቁርአንና 50 ሺሕ ብር ዕርዳታ መስጠታቸውን ራሳቸው አቶ ጁነዲን በጻፉት ደብዳቤ አረጋግጠዋል፡፡

ባለቤታቸው አምባሳደሩ የሰጡትን 50 ሺሕ ብር ለመቀበል ኤምባሲ ሄደው ተቀብለው ሲወጡ፣ ለሽብር ተግባር የሚውል ገንዘብ ተቀብለዋል በሚል ተጠርጥረው በቁጥጥር ሥር መዋላቸው መዘገቡ ይታወሳል፡፡ አቶ ጁነዲን በጻፉት ደብዳቤ ግን ባለቤታቸው የተከበሩ የቤት እመቤት መሆናቸውን ገልጸው ነበር፡፡

በዚህም ምክንያት በኦሕዴድ ሥራ አስፈጻሚ ስበሰባ ላይ በተደረገው ግምገማ፣ ከሥራ አስፈጻሚነት ተነስተው በተራ አባልነት እንዲቀጥሉ መወሰኑን ምንጮቹ አረጋግጠዋል፡፡

ድርጅቱ የ2004 ዓ.ም. በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸምን አንድ በአንድ የገመገመ መሆኑን የገለጹት ምንጮች፣ በፀጥታው ዘርፍ በተለይ ቦረና አካባቢ ተፈጥሮ በነበረው ግጭት ላይ ድክመት መታየቱንና ወደፊት ሊታሰብበት እንደሚገባ ሰፊ ውይይት እንደተደረገበት ተናግረዋል፡፡

በሪፖርቱ ላይ የታዩትንና ድክመት ያለባቸውን አንዳንድ የሥራ ዘርፎች በቀጣይ እንዲስተካከሉ ሐሳብ ተሰጥቶ ጉባዔው መጠናቀቁ ታወቋል፡፡ በድርጅቱ ውስጥ ያሉ አመራሮች እንዳሉ እንዲቀጥሉ ከማድረግ ውጭ ከኃላፊነቱ የተነሳም ሆነ የተሾመ አመራር እንደሌለ ታውቋል፡፡

No comments:

Post a Comment