Welcome

"The thing that lies at the foundation of positive change, the way I see it, is service to a fellow human being." - Lech Walesa

Wednesday 12 December 2012

በአመራር ለውጥ የሚናጠው አዳማ የተረጋጋ አስተዳደር እንዲያገኝ ተወሰነ

•    ከተማውን የኦሕዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ ይከታተለዋል
በውድነህ ዘነበ

የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት በየጊዜው በሚካሄድ የአመራር ለውጥ መረጋጋት ለተሳነው አዳማ (ናዝሬት) ከተማ የተረጋጋ አስተዳደር እንዲኖረው የሚያስችል ዕቅድ መንደፉ ታወቀ፡፡ በአዳማ ከተማ በሦስት ዓመት ጊዜ ውስጥ ብቻ አራት ከንቲባዎች ከሥልጣናቸው ተነስተዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በአስተዳደሩ ሥር በሚገኙ መሥሪያ ቤቶች በተለያዩ እርከኖች ላይ የሚገኙ አመራሮችም ከቦታቸው ተነስተዋል፡፡

ይህ ከፍተኛ ሹምሽር ከተማው የሚፈልገውን ዕድገትና ለውጥ ማምጣት እንዳያስችል አድርጓል በሚል፣ የክልሉ መንግሥት የከተማው አስተዳደር የተረጋጋና ብቃት ያላቸው አመራሮች እንዲመድቡ ከተማው ከክልሉ መንግሥት የበጀት ድጋፍ የሚያገኝበትን መንገድ ቀይሷል፡፡

በዚህ ዕቅድ መሠረት ክልላዊ መንግሥቱ ከሁለት ሳምንት በፊት የከተማው ከንቲባ የነበሩትን አቶ ጉታ ላንቾሬንና ምክትላቸውን ከሥልጣን አንስቷል፡፡ በምትካቸው በፌዴራል ደረጃ በሚኒስቴር ዴኤታ ማዕረግ የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ የነበሩትን አቶ በኩር ሳህሌ ሾሟል፡፡

አቶ በኩር ሳህሌ የኦሕዴድን ማዕከላዊ ኮሚቴ ይሁንታ አግኝተው የተሾሙ ሲሆን፣ አስተዳደራቸውን ማዕከላዊ ኮሚቴው በቅርበት ይከታተለዋል ተብሏል፡፡ የአዳማ ከንቲባ ሆነው የተሾሙት አቶ በኩር በየደረጃው ያሉ የወረዳና የቀበሌ አመራሮች የሁለተኛውን የሦስት ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ ያስጀመሩ ሲሆን፣ ግምገማው ለሁለት ሳምንት ይቆያል ተብሏል፡፡

በግምገማው የተደረሰበት ነጥብ ከሕዝቡ ጋር ምክክር ከተደረገበት በኋላ ጥፋት አለባቸው የሚባሉ አመራሮች ዕርምጃ ሊወስድባቸው እንደሚችል ምንጮች ገልጸዋል፡፡ ከዚህ የአመራር ለውጥ በተጨማሪ አዳማ ከተማ ከክልሉ መንግሥት የበጀት ድጋፍ እንዲደረግለት ተወስኗል፡፡

በተለይ በቅርቡ የክልሉን የበጀት ድጋፍ ያገኛሉ ተብሎ በግንባር ቀደምትነት ከተቀመጡት የአዳማ ከተማ ፕሮጀክቶች መካከል የከተማውን የመጠጥ ውኃ እጥረት ለመቅረፍ የተቀመጠው ዕቅድና ከተማውን ከዓመት ዓመት እየመታ የሚገኘውን ጎርፍ በዘላቂነት ለማስወገድ የተቀመጠው ዕቅድ ይገኙበታል፡፡


የአዳማን የመጠጥ ውኃ ችግር ለመቅረፍ የ800 ሚሊዮን ብር ፕሮጀክት፣ የጎርፍ ችግሩንም ለመፍታት 90 ሚሊዮን ብር የሚያወጣ ፕሮጀክቶች ተግባራዊ ይደረጋሉ ተብሏል፡፡ ከ300 ሺሕ ሕዝብ በላይ ያለው አዳማ ከተማ ከኦሮሚያ ትላልቅ ከተሞች ግንባር ቀደሙ ነው፡፡ የክልሉ መንግሥት መቀመጫ አዲስ አበባ ቢሆንም የክልሉ ምክር ቤት (ጨፌ) የሚገኘው በአዳማ ነው፡፡ የክልሉን ትላልቅ ኮንፈረንሶችና እንቅስቃሴዎች የሚያስተናግድበት አዳማ ከተማ የመልካም አስተዳደርና የሙስና መንሰራፋት ያለበት መሆኑ በሰፊው ይነገራል፡፡

No comments:

Post a Comment