Welcome

"The thing that lies at the foundation of positive change, the way I see it, is service to a fellow human being." - Lech Walesa

Tuesday 3 July 2012

ሀገር በምን ይፈርሳል? 2 .... Temesegen Desalrgn

ከዚህ ቀደም ‹‹ሀገር በምን ይፈርሳል?›› በሚል ርዕስ የዚህን ፅሁፍ የመጀመሪያ ክፍል ፅፌ ነበር። በዚያ ፅሁፍ ላይ ያነሣሁት አንጓ ዘውግ ተኮር የሆነው ፌደራሊዝም ከዕለታት አንድ ቀን ሀገር ማፍረሱ አይቀሬ መሆኑ ላይ ነው። ለዚህም እንደ ‹‹ሠርቶ ማሳያ›› የጉራፈርዳ፣ የጋምቤላ እና የሲዳማ ችግሮች ሊወሰዱ እንደሚችሉ ተነጋግረንባቸዋል። በዚህ ፅሁፍ ደግሞ ከዘውግ ተኮር ፌዴራሊዝሙ በተጨማሪም ዜጎች ‹‹ሀገሬ›› ብለው በሀገራቸው ላይ መተማመን ካልቻሉ ‹‹ሀገር ሊፈርስ›› እንደሚችል እንነጋገራለን። በእርግጥ ይህን ርዕሰ ጉዳይ ደግሜ ለማንሳት ሌላኛው ምክንያቴ ከስርዓቱ የሃሳብ ‹‹ቀሳውስቶች›› ዋነኛው የሆኑት አቦይ ስብሃት ነጋ ሰኔ 16 ቀን 2004 ዓ.ም ከ‹‹አዲስ ጉዳይ›› መፅሔት ጋር ያደረጉት ቃለ መጠይቅ ነው፡፡
ከአጀንዳችን በፊት…
ባለፈው ሳምንት በወጣችው ፍትህ ላይ ‹‹አልሸባብ›› ከሚባል የሽብር ድርጅት ጋር ጋዜጣዋን ለማቆራኘት ስለተደረገው ከንቱ ሙከራ አንድ ፅሁፍ ፅፌ እንደነበር ይታወሳል። በፅሁፉ ላይም የዚህ እኩይ ምግባር ‹‹ፊታውራሪ›› አዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደሆነ የራሱን (የአዲስ ዘመን) ህትመት ጠቅሼ ነበር። ይህንንም ተከትሎ በማግስቱ ቅዳሜ (ሰኔ 16/2004 ዓ.ም.) በወጣው አዲስ ዘመን ላይ አዘጋጁ ቁጣቸውን ሲገልፁ እንደ ከዚህ ቀደሙ በብዕር ስም ወይም በገደምዳሜ ለማድረግ እንኳ ጥቂት አልተጨነቁም። በግልፅ እና በድፍረት ነው ሀገር ጥዬ መጥፋት እንዳለብኝ የነገሩኝ። ይህ ማስጠንቀቂያቸውም የታተመው በገፅ 11፣ የፖለቲካ አምድ ላይ ሲሆን አስፈራሪውም የገፁ ም/ዋና አዘጋጅ ሠይፈ ደርቤ ናቸው። ርዕሱ ‹‹ለሀገር ጥፋት ከመኖር…›› ይላል፡፡ በውስጡ ደግሞ እንዲህ የሚል ትዕዛዝና ማስጠንቀቂያ ይዟል፡- ‹‹ምንም እንኳን ፍትህ ሽብር፣ ሽብር፣ አልሸባብ፣ አልሸባብ ብትልም፤ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ የአንጋፋነት ስያሜ እየሰጠች ‹ይችን ሀገር ለቀን አንወጣም› የሚል ሀሳብ በየጊዜው ብታንፀባርቅም ሀገር ከጠፋ በኋላ መቀመጫ እንደሌላት አለመጠርጠሩ ያስፈግጋል።… መሰደድና እንደገና የልማት ‹ሀሁ…› ውስጥ መግባት አንፈልግም። ከአዲስ መጀመርን አንሻም፤ በእምነት ሽፋን በየጊዜው የውዥንብር አጀንዳ በመቅረፅ ወሬ መፍጠር፣ የተፈጠረውን ወሬ ዜና ማድረግ፣ ሲሻ በእምነት ሽፋን፣ ካልሆነ በጦር ኃይል፣ አልሆን ሲል በመምህራን ጉዳይ፣ እንዲያ ሳይሆን በግንቦት ሰባት፣ እምቢ ሲል ‹… ጊዜ ለኩሉ› እያሉ መወትወት ብዕረኛም ጋዜጠኛም አያሰኝም። ሀገር መውደድና ለሀገር መኖር እንዲያ አይደለም። ይልቅ ለሀገር ጥፋት ከመኖር ከሀገር መጥፋት ይሻላል።›› (ሠረዝ የእኔ)
የተሠመረበትን አንቀጽ ስናየው ይህ አቋም የመንግሥት ጋዜጣ አዘጋጅ አቋም ይሆናል ማለት ሊከብድ ይችላል። አሳዛኙ ነገር ግን አዘጋጁ በስማቸው ስለሆነ የፃፉት ሳንወድ በግድ ከመቀበል ውጭ የሚኖረን አማራጭ አለመኖሩ ላይ ነው። ይህ ከሆነ ደግሞ የተለያዩ ጥያቄዎች መነሳታቸው አይቀርም፡ ፡ ለምሳሌ ለሀገር ጥፋት ከመኖር ከሀገር መጥፋት ይሻላል ምን ማለት ነው? የምንጠፋውስ ወዴት ሀገር ነው? የሚሉትን ልናነሳ እንችላለን፡፡ (በነገራችን ላይ ይህ ማስጠንቀቂያ ‹‹አልሸባብ ላከው›› ከተባለው ማስፈራሪያ የተለየ አይደለም። ምን አልባት ልዩነት አለው ከተባለ እንኳ የአዲስ ዘመኑ ‹‹ሀገር ለቆ መጥፋት›› የሚል አማራጭ ሲኖረው፤ የአልሸባቡ ‹‹ህይወት እናጠፋለን›› የሚል አማራጭ ማስቀመጡ ብቻ ነው)
የሆነ ሆኖ በፍትህ ላይም ሆነ በእኛ በአዘጋጆቹ ላይ ለሚደርስ አንዳች ‹‹ክፋት›› እኚህ የጋዜጣው አዘጋጅም ሆኑ ማስጠንቀቂያውን በሚያዘጋጁት የፖለቲካ አምድ በኩል እንዲያደርሱ የላኳቸው ‹‹ሰዎች›› አስቀድመው ሀላፊነቱን ወስደዋል፡፡ መቼም ከዚህ የበለጠ መንግስታዊ የሽብር ድርጊት የትም ተሠምቶ እንደማያውቅ እርግጠኛ ነኝ፡፡ አልቃይዳ እና አልሸባብ እንኳ አደጋ ሲጥሉ እንዲህ ግልፅ ማስጠንቀቂያ ሠጥተው የሚያወቁ አይመስለኝም፡፡ እንግዲህ የሚሆነውን እናያለን፡፡ አሁን ወደ አጀንዳችን እንመለስ።
ሀገር በምን ይፈርሣል?
በእርግጥ ይህ ጥያቄ አይደለም። በተግባር እየታየ ያለና ሊሆን የሚችል አደጋ ነው። የሀገሪቱን የፖለቲካ ስልጣን ከጨበጠ ሃያ አንድ ዓመት የሞላው ኢህአዴግ ከፖለቲካው ባሻገር ኢኮኖሚውንም ሆነ ፕሮፓጋንዳውን ‹‹ጉልተ-ርስት›› አድርጎታል፡፡ ይህ ብቻም አይደለም፡፡ ይልቁንም እንዲህ በጉልበት ያከማቸውን ‹‹ኃይል›› እና ‹‹ገንዘብ›› መልሶ ወደ ህዝብ ሲያመጣው ጉዳይ መፈፀሚያ ወይም ድጋፍ ማሰባሰቢያ እያደረገው ነው፡ ፡ ለዚህም ነው ግንባሩ የእኔ ከሚለው ርዕዮተ-ዓለም የተለየ አመለካከት ያለው ከመንግስት የስራ ‹‹ዕድል ፈንታው››ን እንዳያገኝ የሚያደርገው፡፡ ይህ ሰው ተበድሎ ቢከስ ወይም በሀሰት ቢከሰስም አይረታም። በአጠቃላይ ለህዝባዊ አገልግሎት የተቋቋሙ መንግስታዊ አገልግሎት ሰጪ ድርጅቶችም እንዲሁ መስፈርታቸው ከ‹‹ኢትዮጵያዊነት›› ይልቅ ‹‹ኢህአዴጋዊነት›› የሚል ከሆነ ውሎ አድሯል። ልክ ኢህአዴግ የሚባል ዳር ድንበሩ የተከበረ ሀገር ያለ ይመስል።
በተለይም ከምርጫ 97 በኋላ ተራራና ወንዞቹ ሳይቀሩ ‹‹የግንቦት ሃያ ፍሬ ናቸው›› ወደ ማለት አዘንብሏል። ይህም ዕውን ይሆን ዘንድ ማደራጀት፣ ማደራጀት… አሁንም ማደራጀት። አባላትን ማብዛት፣ ማብዛት፣ ማብዛት… አሁንም ማብዛት የሚል ፍልስፍናን እንደዋነኛ አጀንዳ የያዘው፡፡ ሌላው ቀርቶ ከኢህአዴግ ጥቅምም ሆነ ከፖሊሲው ጋር አንዳች ግንኙነት የሌለው ለእስረኞች የሚሰጠውን ‹‹አመክሮ›› ያልተደራጀ እንደናፈቀው ይቀራል የማለት አዝማሚያዎችን እየሰማን ነው። ይህ አይነቱ ‹‹ጥርነፋ›› ደርግ ለመጨረሻ ጊዜ የተፍጨረጨረበትን፣ ነገር ግን ግብአተ መሬቱ ከመፈፀም ያልታደገውን ‹‹ሁሉም ነገር ወደ ጦር ግንባር›› መፈክርን ያስታውሰኛል። …ሁሉም ነገር የኢህአዴግ ነው። ‹‹ከእኔ በቀር ሌላ አምላክ አይኑርህ›› ምድራዊው ትርጓሜ ይህ ነው፤ ሌላ አይደለም፡፡ ከኢህአዴግ በቀር…
ከዚህ ቀደም ፕሮፌሠር መስፍን ወልደ ማርያም በፍትሕ ጋዜጣ ‹‹መሬት መሬት አንድ›› ሲሉ በፃፉት አርቲክል ላይ መሬቱ በሙሉ ለባለሀብት ተሸጦ ካለቀ፤ ቀሪው ኢትዮጵያዊ መሬቱ ቢወረር ለማን መሬት ብሎ አጥንትና ደሙን ይከሰክሳል? የሚል ይዘት ያለው የነገ ስጋታቸውን ገልፀው ነበር። በእርግጥ ፕሮፍ ልክ ናቸው። የጋምቤላን መሬት የተቀራመቱት ህንድና ሳውዲአረቢያም ሆኑ ዋና ዋና የከተሞቻችን እምብርት እየገዛ ያለው መሀመድ አላሙዲ ‹‹ሀገሪቱን በጥቂቶች የመጠቅለል›› ኢህአዴጋዊ ፍልስፍናን ከዳር እያደረሱት ይመስለኛል። የእነዚህ ሁሉ ድምር ውጤትም ነው ሀገር የሚያፈርሰው። …ሀገር ህልውናዋ የሚረጋገጠው ዜጎች ‹‹ሀገሬ›› ሲሉ እንጂ የጥቂት ጉልበተኞች ‹‹ማረሻና ማጭድ›› ስትሆን አይደለም። አሁን እየሆነ ያለው ግን በግልባጩ ነው። ከዚህም በመነሳት ነው ‹‹አይበለውና!›› እንደቀድሞዎቹ ቀውጢ ጊዜያት የሀገሪቱ ሉአላዊነት ቢደፈር ማን ይሆን ‹‹ሀገሬን ዳር ድንበሬን›› ብሎ የሚሞተው? በሚል ስጋት የተዋጥነው፡፡ መቼም አላሙዲ እና የካራቺ ሩዝ አምራች ገበሬዎች ‹‹ኢትዮጵያ የእኛ መመኪያ…›› እያሉ ሊዘምቱ እንደማይችሉ ግልፅ ነው።
በ ጋ ም ቤ ላ - ፓ ኪ ስ ታ ና ዊ ያ ን ፤ በኡጋዴን-ቻይናውያን የተገደሉት ምክንያትም ምልክቶች ሊሰጠን ይችላል፡፡
እናም መሬትን ያህል ነገር ቀርቶ ጥቃቅን የዜግነት ጥቅሞቹን በጠየቀ ቁጥር ‹‹የፓርቲ አባል ነህ? ወይስ አይደለህም?›› በሚል ማንፈሻ የሚንገዋለለው ኢትዮጵያዊ እንደከዚህ ቀደሙ ባንዲራ ለብሶ ሊዘምት ይችላል ማለቱ ገራገርነት ነው። ጥላሁን ብርሃን ስላሴ ቤተ ‹‹የ20ኛው ክፍለ ዘመን ኢትዮጵያ-ክፍል አንድ›› በሚል ርዕስ በፃፉት መፅሕፍ ላይ በ1928ቱ የፋሽስት ጣሊያን ወረራ ጊዜ ከቤልጅግ ሀገር ተገዝቶ የመጣው የጦር መሣሪያ ለወታደሮች ሊከፋፈል ሲል ራስ ካሣ ወታደሮቹ መሳሪያውን ይዘው ወደጦር ሜዳ ላይሄዱ ይችላሉ ብለው በመስጋት እንዳይታደላቸው ተቃውመው እንደነበረ ይገልፃሉ።
‹‹ሃሳባቸው ወታደር መሣሪያውን ይዞ ተፈሪን ይከዳል ብለው በመጠርጠር ነው፡፡ ለዚህም ምክንያቱ ወታደሩ በወር የሚከፈለው ሦስት ማርትሬዛ ብር (ጠገራ ብር) ስለኾነና ቅሬታ ስለነበረው ነው። ወታደሮቹም፡-
‹እንደራበኝና እንደሞረሞረኝ
ከጠገበው ጋራ ልሞት ነው መሰለኝ›
ብለው ዘመቱ ይባላል›› ሲሉ ጽፈዋል። እኔም ይህን ነው እያልኩ ያለሁት። ‹‹ከመንግስት ቤት›› እስከ ‹‹መንግስት ስራ›› ማግኘት የዜግነት ሳይሆን የፓርቲ መብት ከሆነ፤ የመከላከያም ሆነ የፌዴራል ሠራዊቱን ከሚተማመንበት ይልቅ የሚፈራው ከበረከተ፣ የስለላ መዋቅሩ ከፓርቲ መዋቅር ካልተለየ፣ የፍትሕ ስርዓቱ የድርጅት ግምገማን ከመሠለ… አባቶቻችን በደም- በአጥንታቸው ያቆዩልንን የምንወዳት ሀገራችንን ሊያፈራርስ ጉልበት ካለው ማዕበል አንዳች ኃይል አያቆመውም፡ ፡ የአቶ በረከት ስሞዖን ‹‹የሁለት ምርጫዎች ወግ›› መፅሀፍም ቢሆን እንኳ-አይቻለውም። (ይህን ያልኩበት ምክንያት በረከት፣ ፓርቲያቸውን በጉልበቱ ከተሰቀለበት የስልጣን ማማ ሊያወርደው ጥቂት ቀርቶት የነበረውን ሱናሚ ምርጫ 97 ‹‹ናዳ›› ሲሉ ከገለፁ በኋላ፣ የጎዳና ላይ ግድያውን፣ የጋዜጠኞችና የፖለቲከኞችን ጅምላ እስር ጨምሮ ሲቪል ተቃውሞን ደምስሰው ‹‹አውራ ፓርቲ›› የተሆነበትን ቀመር በዚሁ መፅሃፍ ‹‹ናዳን የገታ ሩጫ›› ሲሉ በማንቆለጳጰሳቸው ነው)
በእርግጥ ሀገር የመታደጉ ጊዜው የረፈደ ቢመስልም ጥቂት ወራት ወይም አመታት ይቀሩታል። ይህ ሊሆን የሚችለው ግን ከኢትዮጵያዊነት ይልቅ ‹‹ኢህአዴጋዊነት››ን በማስቀደም አይደለም። ወይም ‹‹ታግዬ ጥዬአለሁና ሀገር ምድሩ የግል ርስቴ ነው›› በሚል ፍልስፍናም አይደለም። ይህ የተሳሳተ ፍልስፍና መሆኑ ያልገባው ካለ ምናልባት ከአፄ ምኒልክ አስተዳደር መማር ይቻላል። መማር ለፈለገ ማለቴ ነው። ከዛው ‹‹የ20ኛው ክፍለ ዘመን ኢትዮጵያ- ክፍል አንድ›› መጽሐፍ ላይም እንዲህ የሚል ምርጥ የአስተዳደር ምሳሌ ልናገኝ እንችላለን፡-
‹‹አፄ ምኒልክ የግል መሬት እንዲይዙ ተብለው ሲመከሩ ‹መላው ኢትዮጵያ የማን ኾነና እኔ በግሌ መሬት እይዛለሁ?› ብለው በመመለሳቸው በምኒሊክ ስም የተያዘ አንድም መሬት አልነበረም። የእናታቸውን የዘር ርስት ወራሽ ቢሆኑም ገበሬው እያረሰ ሲሆን፣ በግብር ምክንያት ከምስለኔው ጋር ተጋጭተው ጉዳዩ አፄ ምኒልክ ዘንድ ሲቀርብ ‹ፈጣሪዬ የመላ ኢትዮጵያ አባት ስላደረገኝ እሡም ከልጆቼ አንዱ ስለሆነ በስሙ ሊገበር ይችላል› ብለው መረቁለት፡ ፡›› በእርግጥ ይህ ድንቅ የአስተዳደር ዘይቤ ቢሆንም ከዚህ በተቃራኒው የሚቆም ታሪክም አለን፡፡
የዚህ ታሪክ ባለቤት በታሪካችን ከተጠቀሱት ገብጋባ ንጉሶች አንዱ ነው፡ ፡ ንግስናውም በአክሱም ዘመን ሲሆን ስሙም ዞስካለስ ይባላል፡፡ እንደታሪካችን ትርክት ዞስካለስ ለሀገራችን የመጀመሪያው ወይም ‹‹Known›› ንጉስ ነው፡፡ ‹‹THE PERIPLUS OF ERYTHREAN SEA›› በሚል ርዕስ በዘሙኑ የተፃፈ መፃሀፍ ይህንን ንጉስ ‹‹Greedy Merchant›› (ገብጋባው ነጋዴ) ሲል ይገልፀዋል፡፡ ይህ ንጉስ የነበረው ከክርስቶስ ልደት በኋላ በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን አጋማሽ ነው፡ ፡ ከዚህ አንፃር ነው ወደኋላ 2ሺህ አመት ተጉዘን ከዞስካለስ ከመማር በህይወት ካለፉ በቅጡ መቶ አመት እንኳን ካልሞላቸው ምንሊክ መማሩ የተሻለ ነው የምለው፡፡ …ለእኔ መንግስት ማለት እንደ ምንሊክ ያለ አስተዋይ እንጂ እንደ ጥንቱ ዞስካለስ ያየው የሚያምረው ‹‹ቆንቋና›› ነጋዴ አይደለምና። ስለዚህም ይህ ሁኔታ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ ምንሊክ ካደረጉት የተለየ ትርጉም ሊኖረው አይገባም። እንደዕድል ሆኖ ግን በመሬት ያለው የዚህ ተቃራኒ ነው። እናም በህዝብ ሀብት የጋራ መኖሪያ ቤት (ኮንዶሚኒየም) ገንብቶ ሲያበቃ እንደ ስስታም ነጋዴ አትርፎ መሸጥ በየትኛውም መንገድ ‹‹ልማታዊ›› ሊያስብል አይችልም፡፡ አርባ አመት ግብር ሲከፍል የቆየ ነጋዴን ከቦታው እንዲነቀል ተደርጎ ሲያበቃ ‹‹ለመንግስት ቤት ምትክ አንሰጥም›› ማለቱም ማጅራት ከመምታት በምን ሊለይ እንደሚችል ግልፅ አይደለም፡ ፡ የፖለቲካ ስርዓቱ የወለደው የድርጅትም ሆነ የግለሰብ ነጋዴ፣ ከለፍቶ አዳሪው ነጋዴ በተለየ ሁኔታ ከታየ መቼም ቢሆን እንደአስተዳደር አምኖ መቀበሉ ድንገት ሀገር ሊያፈርስ የሚችልበት አጋጣሚ ለመብዛቱ ጥርጥር የለውም። ነጋድረስ ገብረ ህይወት ባይከዳኝ ‹‹መንግሥትና የሕዝብ አስተዳደር›› በሚለው መጽሐፋቸው ይህንን ሃሳብ እንዲህ ሲሉ ያጠናክሩታል።
‹‹በያንዳንዱም መንግሥት የሚያድሩ ብዙ ልዩ ልዩ ነገዶች ይኖሩ ይሆናል። ስለሆነም መንግሥት አንዱን ነገድ አጥቅቶ ሌላውን ነገድ ለመጥቀም ሥራው አይደለም። አስተካክለን ካሰብን ዘንድ መንግስት መቆሙ ለሕዝቡ ሁሉ ጥቅም ነው። መንግስት ህዝቡን ሁሉ በትክክል ለመጥቀም ካላሰበ መንግሥት በዙፋኑ ሊቆም አይችልም። ላንዱ ነገድ ወይም ለጥቂት ሰዎች ብቻ ማድላት ለመንግሥት የሚገባ ሥራው አይደለም።››
እኔም ይህንን ነው እያልኩ ያለሁት ‹‹ለጥቂት ሠዎች ብቻ ማድላት ለመንግሥት የሚገባ ሥራው አይደለም።››እኔም ይህንን ነው እያልኩ ያለሁት ‹‹ለጥቂት ሠዎች ብቻ ማድላት ለመንግሥት የሚገባ ሥራው አይደለም።›› የነጋድራስን ምክር አስተውለን በዚህ ዘመን መንፈስ እንፈክረው ካልን ደግሞ ‹‹ይህ አይነቱ አድልኦ አልፎ ተርፎም እንዲህ የምትሟሟቱበትን ዙፋን በህዝባዊ አብዮት ወደታሪክነት ይቀይረዋል›› የሚል ሆኖ እናገኘዋለን፡፡
ከዚህም ባለፈ ለስርዓቱ ዕድሜ መራዘም ሲባል የረዥም ዘመን ታሪክ ተጋሪ በሆኑ ዜጎች መካከል ‹‹መናፍቃዊ›› ስርዓት ማንበሩ ሀገር ከማፍረስ ውጭ የሚፈይደው ነገር የለም፡፡ ይህ አንድ እውነት ቢሆንም በግሌ ‹‹የሀገራችን አንድነት የፀናው የብሔር ብሔረሰቦች መብት እስከመገንጠል በመከበሩ ነው›› የሚለው የአቦይ ስብሓት ትንተና ውሃ የሚቋጥር ሆኖ አይሰማኝም። ነገር ግን አቦይ ከላይ በጠቀስኩት ቀን በወጣችው አዲስ ጉዳይ መጽሔት ላይ ‹‹ሀገር ማለት ለእርስዎ ምንድነው?›› በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ ‹‹ሀገር ማለት ህዝቡ ነው። የህዝቡ ታሪክ ነው። ትናንት የነበረበት አሁን ያለበት፣ ወደፊት የት እንደሚደርስ ማሰብ ነው›› ካሉት ማብራሪያ ጋር ችግር የለብኝም። ሆኖም ‹‹ሀገሪቱ ልትፈርስ መሆኑ ነው ይህን አንቀጽ (39) የወለደው?›› ለሚለው የመፅሔቱ ጥያቄ ‹‹አይደለም፡፡ እኛም የታገልንበት ነው፡፡ የኢትዮጵያን ሁኔታ ያንፀባርቃል። ነገር ግን ከገመትነው በላይ ሀገር ፈርሳ አገኘናት። ወዲያው የመገንጠል ፍላጐት ከገመትነው በላይ ነው የሆነው። ኢትዮጵያ በምትባል ሀገር መቆየት የማይፈልጉ ብዙ ድርጅቶች ነበሩ። ‹እስከ መገንጠል› የሚለው ነገር ሀገሪቱን አቆይቶልናል። ባለፉት መንግስታት በተሰራበት ግፍ አሁንም ህዝቡ ያለው ምሬት ቀላል አይደለም…›› ያሏት ደንገርጋራ ሃሳብ ብዙም አትመችም። ባይሆን ከዚሁ ጋር አያይዘው የተናገሯት ቁም ነገር ከብዙሃኑ አተያይ ጋር የሚያሰልፋቸው ከመሆኑም ሌላ ጥቂት ተጨማሪ ነገሮች ቢደመሩበት ኖሮ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እያሰሱት ያለውን አትኩሮት በተሻለ ሁኔታ ይስብላቸው ነበር።
አቦይ እንዲህ ነው ያሉት ‹‹አሁንም ቢሆን በዴሞክራሲያዊ ስርዓቱና ልማቱ ካልተፋጠነ ችግር ውስጥ መግባታችን አይቀርም›› እኒህ አንጋፋ ታጋይ አንዳንዴ በጣም ግልፅ ናቸው፡፡ ከማንም በተሻለ ስለዲሞክራሲ እና ልማት የሚወራው ፕሮፓጋንዳ እንደሆነ ያውቃሉ፡ ፡ ጠንቅቀው ስለሚያውቁም ነው ችግር መከሰቱ አይቀሬ እንደሆነ በዘወርዋራ የነገሩን። (ዳሩስ! ዳገት ወቶ፣ ቁልቁለት ወርዶ ካነበረው ስርዓት እየተገፋ ያለ ሰው ከዚህ የበለጠ ምን ሊል ይችላል? መቼም በግልፅ ልማት የለም እንዲሉን ከጠበቅን ፖለቲካ አልገባንም ማለት ነው)
በእርግጥ አቦይ የረሱት ነጥብ የተፋጠነ ልማት ቢኖር እንኳ ተጠቃሚው ‹‹ጥቂቶች›› ከሆኑ የፈሩት ችግር መድረሱን አለማመላከታቸው ላይ ነው፡፡ ጥቂት የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት፣ የአጋር ፓርቲ ወሳኝ ሰዎች እና ብልጣ ብልጥ ነጋዴዎች ቁመናው ያማረ፣ ዛላው የተንዥረገደ፣ በመስታወት ያበደ ሕንፃ ባለቤት መሆናቸው በሀገሪቱ ልማት አለ የሚያስብል አይደለምና፡፡ በተቀረ አቦይ ከህወሓት የአመራር አባልነት ጡረታ ከወጡ ወዲህ ከበርካታ ‹‹እንጀራ ፈላጊ›› ምሁራኖች የተሻለ ድፍረት እና ሕዝባዊ አቋም እየያዙ መጥተዋል (ለመጽሔቱ በሰጡት ቃለ መጠይቅ ውስጥ በሌላ ጊዜ የምመለስበት ሊፍታቱ የሚችሉ ጥቆማዎች እንዳሉ አልክድም)
በነገራችን ላይ አቦይ በቃለ- መጠይቁ ወቅት የሳቱት ግዙፍ ነጥብ (ግንቦት ሃያ በድል አዲስ አበባ ሲገቡ) ‹‹ከገመትነው በላይ ሀገር ፈርስ አገኘናት›› የምትለዋ ነች። እውነት ለመናገር ይህን መቀበል ያዳግታል፡፡ ምክንያቱም ደርግ ሁሉንም ችግር፤ በጦር መሳሪያ የሚፈታ ሕግ የማይገዛው መንግሥት መሆኑ አያከራክርም። በዚህ ግልባጭ ደግሞ ደርግ 17 ዓመት ሙሉ አንድም ስልጣኑን እንዳያጣ፤ ሁለትም ሀገሪቷ እንዳትፈርስ ሙሉ በሙሉ ወደ ጦርነት ሊገባ መቻሉን ልናነሳ እንችላለን። ይህ ሁኔታ ሲብራራ ከኢህአፓ፣ ከህወሓት፣ ከኦነግ እና ከመሳሰሉት ጋር የነበረው ጦርነት የስልጣን ጥያቄ ሲሆን፤ በኤርትራ ምድር ከሻዕቢያ ጋር የነበረውን ግን ሀገር ለማዳንና ለመገንጠል የተደረገ ሆኖ እናገኘዋለንና። ለዚህም ነው የአቦይ ‹‹ሀገር ፈርሳ አገኘናት›› ምላሽ በጲላጦሳዊ ብልጠት የተለበደ የሆነብኝ፡፡
ሌላው ቀርቶ አቦይ የሚኩራሩበት የመገንጠል መብት የሚፈቅደው አንቀፅ ለሁሉም ኢትዮጵያዊ የሚሰራ አይደለም፡ ፡ ለምሳሌ ደቡብን ብንወስድ በርካታ ብሄሮች በዞን ተካፋፍለው በአንድ ክልል ታስረው እናገኛለን፡፡ ሲዳማ ዞን፣ ስልጤ ዞን፣ ወላይታ ዞን፣ ጉራጌ ዞን… የመሳሰሉትን፡፡ እናም በሕገ-መንግስቱ መሰረት መገንጠል የሚሉት የተከለለ መልክዓ-ምድራዊ አቀማመጥ ያላቸው ብሔር፣ ብሔረሰቦች አልያም ህዝቦች ናቸው። የደቡብ ብሔር ብሔረሰብ ክልል ከአንድ ወጥ ብሄር አልያም ብሔረሰብ አለመዋቀሩ እንደ ክልል ‹‹ልገንጠል›› ቢል እንኳ የማይቻለው ነው። እንደ ብዙ ፀሐፊዎች ትችትም የዚህን አንቀፅ መኖር ተማምነው ጥያቄያቸውን ለመግፋት የሚሞክሩትን ‹‹በጠባብነት›› እየከሰሰ ራሱን ሀገር አረጋጊ አድርጎ ከማቅረብ በዘለለ ዕውናዊ ፋይዳውም ብዙ አይደለም።
ምክንያቱም ከእነዚህ ብሄሮች አንዳቸው ‹‹ልገንጠል›› የሚል ጥያቄ ቢያነሱ ህገ-መንግስቱ ራሱ ይደፈጥጠዋል፡፡ ህገ-መንግስቱ የመገንጠል ጥያቄን የሚፈቅደው በክልል ምክር ቤት የሁለት ሶስተኛውን የድጋፍ ድምፅ ሲያገኝ ነውና፡፡ ይህ ሁኔታ ነው አንቀፅ 39ን በራሱ ኢ-ፍታሃዊ የሚያደርገው፡፡ መቼም ከዚህ ከተነሳን ‹‹የብሄር ብሄረሰቦች መብት እስከመገንጠል›› ምፀት መሆኑ አይቀሬ ነው፡፡
የሆነ ሆኖ በሀገራችን ‹‹የእኔነት›› ስሜት የሚሰማን ጎጣችን ተጠቅሶ በታደለን የቀበሌ መታወቂያ አይደለም። ከዚህም በላይ ከሀገራችን ሃብት ፍትሃዊ በሆነ መልኩ መጠቀም የማንም ስጦታ ሳይሆን መብታችን መሆኑ በአፋዊ ሳይሆን በተግባር ሊረጋገጥ ይገባዋል፡፡ የኢህአዴግን ርዕዮተ- አለም ሳንከተል፣ በየትኛውም መዋቅር ሳንደራጅ ቤት፣ ንብረት፣ ስራ፣ ብድር እና የመሳሰሉት ወሣኝ ነገሮች የግድ እንዲመቻቹልን መጠየቅም እንችላለን። ይህንን ጥያቄ መጠየቅም ሆነ፣ ማስተዳደር አልቻላችሁምና ‹‹ስልጣን ልቀቁ›› ማለቱም ተፈጥሮአዊ እና ህገ-መንግስታዊ መብታችን ነው። ጥያቄውን ይዞ አደባባይ መውጣቱም እንዲሁ መብታችን ነው፡፡ …እነዚህ እነዚህ መብቶችን መደፍጠጡ ወይም ለመደፍጠጥ መሞከሩ ደግሞ አመንም አላመንም ሃገር ማፍረሱ አይቀሬ ነው፡፡
ሌላው ሀገር ሊያፈርስ የሚችለው ‹‹ካምሱር›› በአገር ጉዳይ ተቀራርቦ የመነጋገር ፍላጎትን ለመገደብ የሚደረገው ሙከራ ነው፡፡ ዜጎች ይህንን ልማድ እንዲያዳብሩ አስትዋፅኦ ማድረግ ከመንግሥት የሚጠበቅ ግዴታ ነው። ይህን ማድረጉም ሀገርን ካልታሰበ አደጋ ይጋርዳል። በተቀረ አሁን ኢህአዴግ እያደረገ ያለውን ሌሎች አምባገነኖችም አድርገውት ከሽፎባቸዋል። የሚያሳዝነው ነገር ግን ሙከራቸው አለመስራቱን ያረጋገጡት የማይታረም ስህተት ከሠሩ በኋላ መሆኑነው። … ወደተረት-ተረት ከተቀየሩ በኋላ… በሀገራችንም አፄ ኃይለስላሴ ተማሪዎችን ለማፈን ሞክረዋል። አፄው በሀገር ጉዳይ እርስ በእርስ መነጋገርን ለማፈን የቻሉትን ያህል ቢያደርጉም ከ66ቱ አብዮት ሰይፍ ሊያመልጡ አልቻሉም። ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማርያምም እንዲሁ በተመሣሣይ ሞክረው ከሽፎባቸዋል። ለዚህም ነው ኢህአዴግ በሰላዮች ብዛት እና በቻይና ቴክኖሎጂ የተሻልኩ ‹‹አፋኝ›› እሆናለሁ የሚለው ምኞቱ ቀቢፀ-ተስፋ ነው እያልኩ ያለሁት። እንዲያውም ጋዜጠኞችን ከአሸባሪ ጋር ደምሮ ማሰሩን እና የድረ-ገፅ አፈናውን በፍጥነት ካላቆመ ‹‹መጪው ጊዜ ብሩህ ነው›› የሚለው የዝነኛ መፈክሩ ፋይዳ ከተፃፈበት ጨርቅ አያልፍም። ይህ ሁኔታም ነው ሀገር የሚያፈርሰው።
በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባትም ሀገርን በፍቃደኝነት እንደማፍረስ የሚቆጠር ተግባር ነው። በእርግጥ ኢህአዴግ በነቢብ በሃይማኖት ጣልቃ አልገባም ሲል ደጋግሞ ተናግሯል፤ ጽፎአልም፡፡ እንዳሻው በሚያዝበት የመንግስት ሚዲያም እናምነው ዘንድ ብዙ ወትውቷል። አልፎ ተርፎም ወደ ኋላ ተጉዞ በዚሁ ወር በታተመው የንድፈ ሃሳብ መጽሔቱ (አዲስ ራዕይ የግንቦት-ሰኔ 2004 ዓ.ም ዕትም) ላይም የቀድሞ መሪዎች በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባታቸውን ‹‹ውግዝ ከመ አሪዎስ›› ሲል አውግዟል። ‹‹በየዘመኑ የነበሩ ነገስታት እና የበላይ መሪዎች አንዱን ሃይማኖት ከሌላው በሚበላለጥ ሕገ-መንግስታዊ እውቅናና ጥበቃ የነበረው ግፍ ሲፈፅሙ ኖረዋል። መንግሥታዊ ሃይማኖቶች እንዲኖሩ በሕገ-መንግስት በመደንገግ፣ ሃይማኖትና ትምህርትን በማዋሃድና መሪዎቹ የሚፈልጉት ሃይማኖት የህግ ልዕልና እንዲያገኝ በማድረግ የሌሎች እምነቶች ተከታዮች የሚሸማቀቁበትን ስርዓት በመፍጠር ለበርካታ ዘመናት ሕገ-መንግስታዊ የተደረገለትና እውቅና የነበረው መድሎ አስፍነው ቆይተዋል›› ይላል-ኢህአዴግ።
ይህ እውነት ነው። በተለይም አፄ ኃይለሥላሴ ከመንበራቸው እስኪወርዱ ድረስ ሀይማኖት እና መንግሥት የተለያዩ አልነበሩም። ‹‹መንግሥታዊ›› የሚባል ሃይማኖት ነበርና።
ሆኖም ‹‹ጉድ በል ጎንደር!›› የሚያስብለን ግን ‹‹መንግሥትና ሃይማኖት እንዲነጣጠሉ ተደርጓል። መንግስት በሃይማኖት፣ ሃይማኖትም በመንግሥት ጣልቃ አይገባም። ሕገ- መንግስታችን ሃይማኖትና መንግሥት የተለያዩ እንደሆኑ በመደንገጉ ዜጎች የትኛውንም ሃይማኖት ወይም ሴክት መከተል እንዳለባቸው እና በምን መንገድ መከተል እንዳለባቸው መንግሥት መወሰንና አቅጣጫ ማስቀመጥ አይችልም። …በምንም መልኩ ግን መንግስት ሃይማኖት ሊያስተምር አይችልም። ይህን ተከተሉ ያንን አትከተሉ ማለት አይቻልም። እስከአሁን ባለው ተግባሩም ሆነ ከታገለለት መርህ አንፃር ኢህአዴግም ሆነ በእሱ የሚመራው መንግሥት ይህን ሊያደርጉ አይችሉም። ይህ የሆነበት ሁኔታም የለም።›› የሚለውን የኢህአዴግን ‹‹ቃል›› በንድፈ ሀሳብ መጽሔት ላይ ስናነብ ነው። ምክንያቱም በዚህ ወቅት እንኳ ቢያንስ ሕዝበ ሙስሊሙ ‹‹መንግሥት ጣልቃ ገባብን››፣ ‹‹የአህባሽን ወይም የወሀቢያ ሴክትን ለመከተል መንግሥት አይመርጥልንም››… የመሣሠሉትን ተቃውሞ ማሰማቱ በግልፅ ጣልቃ መግባትን የሚያሳዩ ናቸውና።
በአጠቃላይ እ.ኤ.አ¸በ2007 ዓ.ም የወጣው የጋሉብ ጥናት ውጤትም የዜጎች በሀገሪቱ ተቋማት ያላቸውን ዕምነት በአስፈሪ ደረጃ እንደወረደ ይናገራል። እንደ ዓለም አቀፋዊው የጥናት ተቋም ዘገባ፣ በፍርድ ቤቶች፣ በምርጫ ፖለቲካ፣ በወታደራዊው ሃይልም ሆነ በእምነት ተቋሞቻቸው ላይ የሚተማመኑ ኢትዮጵያውያን ቁጥር ከሰሃራ በታች ካሉት ሀገራት እጅግ ዝቅ ያለ መሆኑ ሁኔታውን አደገኛ ያደርገዋል። ሁላችንም እንደምናውቀው ደግሞ ዜጎች በሀገራቸው ተቋማት ላይ እምነት ሲያጡ፣ ከዋነኛው የፖለቲካ ተዋፅኦ በመራቅ፣ ነፃነታችንን ነፍገውናል ብለው የሚያስቧቸውን ዓለማዊ ተቋማት ወደ ማፍረስ ይሄዳሉ። እንግዲህ ኢህአዴግ በራሱ አምባገነንነት የተነሳ ሁኔታዎችን ወደዚህ እየገፋ፤ ዜጎች ደግሞ ይህን ለማረም ሌላ መንገድ ሲታያቸው አሸባሪ፣ ሀገር ገንጣይ… እያለ በጡንቻ ለመደፍጠጥ እየሞከረ ነው።
በአናቱም የሁለተኛ ዲግሪ ያላቸውን ዜጎች ‹‹በኮብል እስቶን›› ስራ ማሳተፍን እንደ ምርጥ ‹‹ሞዴል›› በመውሰድ ከተኩራራን፣ የፍትህ ስርዓቱ የፓርቲው አፈ-ቀላጤ ከሆነ፣ የሀገሪቱ አንጡራ ሃብት ከዜጎች ይልቅ የስርዓቱ ቁንጮዎች እና የምንደኞቻቸው ከሆነ፣ ሠራዊቱ ከሀገር ይልቅ ፓርቲውን ካስቀደመ… እውነት እውነት እላችኋለሁ ሀገር በመፍረስ ጠርዝ ላይ ቆመች ማለት ነው፡፡ መቼም አቦይ ስብሃት ነጋ ግንቦት ሃያ ሺ ዘጠኝ መቶ ሰማንያ ሶስት ‹‹ፈርሳ አገኘናት›› ያሏት ሀገር ዛሬ ካለችብት በእጅጉ የምታስመርጥ ነች፡ ፡ ለዚህ ደግሞ ቀላል ማሳያ ማንሳት ይቻላል፡፡ ለምሳሌ በደርግ ጊዜ የነበረችው ኢትዮጵያ ቀይ ባህር ዳር ድንበሯ ነው፡፡ ለአንድ ሃገር ወሳኝ ከሚባሉት ውስጥ ቀዳሚው ወደብ ነው፡፡ ያንጊዜ ደግሞ ኢትዮጵያ የሁለት ወደብ ባለቤት ነበረች፡፡ በአናቱም ከጎሳ ይልቅ ኢትዮጵያዊነት የሚቀድምበት ደጉ ዘመን ነበር፡፡ እናም የሀገር ትፈርሳለች ፍርሃታችን ነፍሳችንን ወጥሮ ቢይዘንም የታሪክ ምሁሩ ፕሮፈሰር ባህሩ ዘውዴ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚክስ ባለሙያዎች ማህበር ያዘጋጅ በነበረው ‹‹ርዕይ 2020›› ላይ ‹‹ኢትዮጵያ በአክሱም ዘመነ መንግስት ውድቀት ማግስት፣ በዘመነ መሳፍንት ወቅት፣ በ1966ቱ አብዮትና በ1983ቱ የሽግግር ዘመን ትፈራርሳለች ተብሎ ብንሳቀቅም እነዚህን ጊዜያቶች ተሻግራለች፡፡ እነዚህ የመከራ ጊዜያትን እንድትሻገር ያስቻላት ጥልቅ የዜጎቿ ማህበራዊ ትስስር ይመስለኛል›› በማለት የተናገሩት ቢያንስ ነገን ‹‹ሀገሬ ትፈርሳለች›› በሚል ፍርሃት እንዳንወጠር ያደርገን ይሆናል፡ ፡ አሊያም ‹‹When dictatorship is a fact Popular uprising is a right›› የሚለውን የፈረንጆች አባባል ከሙሴ አስርቱ ትዕዛዛት የቀጠለ 11ኛው ትዕዛዝ አድርገን በፍፁም ልባችን መቀበላችን አይቀሬ ሊሆን ነው፡፡

No comments:

Post a Comment