Welcome

"The thing that lies at the foundation of positive change, the way I see it, is service to a fellow human being." - Lech Walesa

Friday 6 July 2012

የአእምሮ ክስረት፣ ሁሉም ነገር ሽብርተኛነት!

በኢራቅ፣ በአፍጋኒስታን፣ በፓኪስታን፣ በየመን፣ በአንዳንድ የሰሜን-ምዕራብ የአፍሪካ አገሮች፣ አሁን በቅርቡ ደግሞ በናይጂርያ፣ አልፎ አልፎም በትልልቆቹ የምዕራባውያን አገሮች፣ አልፎ አልፎም በምሥራቅ አፍሪካ በአሜሪካ ኤምባሲዎች ላይ የደረሰው ዓይነት የሽብርተኛነት አደጋ በአፍሪካ ቀንድ አገሮች ላይ እስካሁን ድረስ አልደረሰም ለማለት ይቻላል፤ ሰላም በራቃት ሶማልያም እንኳን ከላይ በተጠቀሱት አገሮች ውስጥ የሚታየው ዓይነት ሽብርተኛነት የለም ለማለት ይቻላል፤ ጦርነትን ከሽብርተኝነት የማንለየው ከሆነ ግንዛቤያችን የተለየ ይሆናል፤ በሕንድ ውቅያኖስ ላይ ሶማልያውያን ቡድኖች የሚያሳዩት የባሕር-ላይ ሽብርተኛነት ፈጽሞ በባሕርዩ የተለየ ነው፤ ለዘረፋና ለገንዘብ መሰብሰቢያ እንጂ ሰዎችን ለመግደል ወይም ለመጉዳት አይመስልም።
ሽብርተኛነት ከዲያብሎስ ፋብሪካ የወጣ፣ የጠራ ክፋት ነው፤ በኢትዮጵያ ባሕርይ ውስጥ ፈጽሞ የለም፤ በኢትዮጵያ ውስጥ የስዒረ-መንግሥት ሙከራዎች ሁሉ የሚከሽፉት ይህ የጠራ ክፋት ስለሌለብን ነው፤ በእርግጥ ሻዕቢያና ወያኔ በሽብርተኛነት አልተጠቀሙም ለማለት አይቻልም፤ ግን እነሱም ቢሆኑ ኢትዮጵያዊ ባሕርያቸው ልጓም ሆኖባቸው የነበረ ይመስላልና በዓይነቱም ሆነ በመጠኑ በጣም አነስተኛ ነበር፤ ምናልባትም አሁን በአዋጅና በተለያዩ ማስፈራሪያዎች የሚሰማው ኡኡታና መሸበር ከራሳቸው ልምድ የተገኘ ይሆናል እንጂ ኢትዮጵያውያን የሽብርተኛነት ጥፋት ያደርሳሉ ተብሎ በመስጋት አይመስለኝም፤ ሽብርተኛነት የሚለፈፈው የፖለቲካ ትርፍ ይገኝበታል ተብሎ ከሆነ ከስሕተት ካለመማር የመነጨ መሆን አለበት።
በ1998 እነሽመልስ ከማል የዓቃቤ ሕጉን ወንበር በአቋራጭ ይዘውት በነበረ ጊዜ ክሱን ለማሳመር የወንጀል ዓይነት እንዳይቀርባቸው ብለው በመጀመሪያ በዘር ማጥፋት፣ ይህ መሳቂያ ሲሆንባቸው ደግሞ ወደዘር ማጥፋት ሙከራ ለውጠውት ነበር፤ በመጨረሻም ይህንኑ ክስ ሁለቱ ዳኞች ከውስጥ ባልወጣ መንፈሳዊ ወኔ ውድቅ አደረጉት፤ በአሁኑ ጊዜ የሽብርተኛነት ሕግና ዛቻ፣ ማስፈራሪያ ሁሉ ምንጩ ያው የዱሮው የወንጀል ፋብሪካ ሳይሆን አይቀርም፤ ማንም ጤናማ ኢትዮጵያዊ ምንም ያህል የፖለቲካ ጥላቻ ቢኖረውና የፖለቲካ ትግሉ የተዳፈነበት መስሎ ቢታየውም፣ ልጆቹ ከትምህርት ቤት ሲወጡ፣ ሚስቱ ከሥራዋ ወይም ከገበያ ስትመጣ፣ ቤተሰቡ በቤተ ክርስቲያን ወይም በቤተ መስጊድ ሄደው ፈጣሪያቸውን ሲማፀኑ በድንገት በቦምብ እንዲቃጠሉ ወይም በጥይት እንዲጠበሱ -- ማንም ጤናማ ኢትዮጵያዊ ይህንን አይመኝም።
ለፖሊቲካ ትርፍ ከሆነ የዘር ማጥፋት ወንጀል መለጠፉ በመጨረሻ አሳፋሪ እንደሆነ ሁሉ የሽብርተኛነት ወንጀልም ከአሁኑ በአገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን በዓለም- አቀፍ ደረጃም መሳቂያ እየሆነ ነው፤ በአገር ላይ፣ በማኅበረሰብ ላይ የሚቃጣ ወንጀል ሁላችንንም የሚያስቆጣን እንጂ የሚያስቀን ወይም ለፌዝ የሚጋብዘን ሊሆን አይገባም፤ ሽብርተኝነትን ሁላችንም አምርረን ስለምንጠላው ልናፌዝበት አይገባም፤ ነገር ግን አንዱ የኢትዮጵያዊ ባሕርይ የማይመስለው ነገር ከላይ ከባለሥልጣኖቹ ሲወረወርበት ማፌዝ ነው፤ በደርግ ዘመን ዜና ማሰራጫዎቹ ስለሻቢያና ስለወያኔ እስቲሰለች የሚያወሩት የማይጥመው ሁሉ ሻቢያና ወያኔ የሚሉትን ቃላት መቀለጃ አድርጎ ‹‹አንተ ሻቢያ… አንተ ወያኔ›› ይባባል ነበር፤ አሁንም ‹‹አንተ ሽብርተኛ›› መባባል እየተጀመረ ነው፤ እንዲህ ሲሆን ሽብርተኛነት የሁላችንም ፍርሃትና ስጋት መሆኑ ቀርቶ የነጌቶች ብቻ ይሆናል።
የማሰብ ችሎታ እንደቆመ የሚያመለክተው የኦሮሞ ነጻ አውጪ ድርጅትም፣ የኦጋዴን ነጻ አውጪ ድርጅትም፣ በአገር ውስጥና በውጭ አገር ያሉ ጋዜጠኞችም፣ ተቀናቃኝ የፖለቲካ ቡድኖችም… ሁሉም በሽብርተኛነት እየተፈረጁ የሚከሰሱ ከሆነ የኢትዮጵያን ችግር ሁሉ አንድ ከረጢት ውስጥ በመክተት ለማቅለል መሞከሩ የችግሩን ውስብስብነትና ከባድነት አይለውጠውም፤ የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚደንት ቡሽን የጡንቻ አስተሳሰብ ለመከተል ቢፈለግም ብዙ ነገሮች ይጎድሉናል!
ለተመስገን ከአል ሸባብ የተላከ አስመስሎ መልእክት የሚልክለት ምን ዓይነት አንጎል በአንገቱ ላይ የተሸከመ ነው? ለፍትሕ ጋዜጠኞችስ በተለያዩ መንገዶች ማስፈራሪያ የሚልከው ምን ያህል የማሰብ ችሎታው የተዳፈነበት ነው? ይህንን የሚፈጽሙት የሽብርተኛነት ጥንስሶች ናቸው።
ከዚህ በፊት ብዙ ጋዜጦችና መጽሔቶች ነበሩ፤ ዛሬ የሉም፤ ግን ሌሎች ቦታቸውን ይዘው ሀሳባቸውን እያሰራጩ ናቸው፤ ገንዘብ እንደልባቸው እያገኙና የፈለጉትን ባለሙያ የመቅጠር ችሎታ እያላቸው፣ ማንኛውም ዓይነት የጋዜጠኛነት መሣሪያ በእጃቸው እያለ፣ የሕዝብ የመገናኛ ብዙኃኑን በሙሉ እየተቆጣጠሩ፣ የሌሎችን ጭልጭል የሚሉ ሀሳቦች በጉልበት ለማዳፈን የሚፈልጉ ወይም ፍርሃታቸው ከመጠን እያለፈ እንቅልፍ ነሥቶአቸዋል፤ ወይም ያልነበረ የአእምሮ ኃይላቸው እየተሟጠጠ አልቆ ጡንቻ ብቻ ሆኖባቸዋል፤ ስለዚህም ሀሳብን በሀሳብ ለመቋቋም አቅም የላቸውም፤ ለዚህ ተጨባጭ ማስረጃ የሚሆነው በብዙ የቴሌቪዥንና የራዲዮ ጣቢያዎች፣ በብዙ ጋዜጦችና መጽሔቶች ከኢትዮጵያ አልፈው በእስያ፣ በአውሮፓና በአሜሪካ ሀሳብ ካላቸው በየቀኑ ማሰራጨት የሚችሉ አገልጋዮች አሉአቸው፤ ይህ ሁሉ የኢሕአዴግ ኃይል በአገር ውስጥ ብቻ ተወስኖ በአጠቃላይ በሳምንት ከሃምሳ ሺህ የማይበልጥ ጋዜጣን በሀሳብ ማሸነፍ ሲያቅተውና በጡንቻው ወደመተማመኑ ሲመለስ ምን ሊባል ነው? ይህ ድካም የአእምሮ ድካም ብቻ አይደለም፤ ውሎ አድሮ የፖለቲካ ድካምም ይሆናል፤ የፖለቲካ ድካም በጊዜው ካልታረመ የውስጥ ችግሮችን መፈለፈሉ ብቻ ሳይሆን ወደውጭም እንደሚዛመት መረዳት አለብን፤ ዛሬ በአእምሮ ስንፍና አንድመልክ እንዲመስልልን በሽብርተኛነት ቀለም የለቀለቅናቸው ሁሉ ሌላ እየሆኑ ሲወጡ መፍትሔ ብለን ያወጣነው የጡንቻና የስንፍና ዘዴ ለጡንቻ የማይበገር ያፈጠጠና ያገጠጠ ችግርን ይወልዳል።
አካባቢያችን በሽተኛ ነውና የኢትዮጵያን ሕዝብ ከሽብርተኛነት ለማዳን አስፈላጊም ተገቢም ነው፤ ዘዴው የኢትዮጵያን ሕዝብ በመከፋፈል፣ በማጋጨት፣ በማስጨነቅና በጠላትነት በመፈረጅ አይደለም፤ ይህ ኮረኮንች መንገድ እያንገላታ የሚያመራው ወደገደል ነው!
ለተመስገን ደሳለኝ አል ሸባብ ደብዳቤ ጻፈለት ብሎ የሚያምን ኢትዮጵያዊ የለም፤ አል ሸባብ ምናልባት ዱሮም ሆነ ዛሬ የሚተዋወቃቸው ኢትዮጵያውያን ይኖሩ ይሆናል፤ እነዚያን ማፈላለግ ያስፈልግ ይሆናል፤ የአል ሸባብንም ሆነ የአል ቃይዳን ወዳጆች በፍትሕ ጋዜጣ አካባቢ ይገኛሉ ብሎ መጠርጠር ደኅንነቱ ወደ እውነቱ እንዳያተኩር ለማደናገር የተፈጠረ የጠላት ዘዴ ነው፤ በበኩሌ የኢትዮጵያን ሕዝብ ደኅንነት አደጋ ላይ የሚጥል የውጭ ኃይል ከየትም መጣ ከየት እቃወማለሁ፤ አይቼ አላልፈውም፤ ኢትዮጵያ የእነዚህ የአእምሮ አቅመ-ቢሶች፣ ሰነፎችና እበላ- ባዮች አገር ብቻ አይደለችምና እኛም ለደኅንነቷ ስለምንጨነቅ የሚሰነዝሩትን ማስፈራሪያም ይሁን ማደናገሪያ አውቀንባችኋል እንላቸዋለን።
የምንታገለው ለኢትዮጵያ ሰላምና ደኅንነት፣ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ነፃነትና እኩልነት፣ ለፍትሐዊ አስተዳደር፣ ለልማትና ለብልጽግና መሆኑ የማይገባቸው እስቲገባቸው ድረስ እንቀጥላለን፤ እነሱ እየተማሩ ወደኛ ይመጣሉ እንጂ እኛ ወደነሱ አንሄድም።

No comments:

Post a Comment