Welcome

"The thing that lies at the foundation of positive change, the way I see it, is service to a fellow human being." - Lech Walesa

Thursday 20 September 2012

ህወሃት አባይ ወልዱን ሊቀመንበር፤ ደብረጽዮንን ምክትል አድርጎ መረጠ

(ኢ.ኤም.ኤፍ) የህወሃት ሊቀመንበር የነበረው አቶ መለስ ዜናዊ ካረፈ በኋላ፤ ህወሃት እና ኢህአዴግ ሊቀመንበር ሳይኖረው መቆየቱ ይታወሳል። ኢህአዴግ አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ሊቀ መንበር አድርጎ ሲመርጥ፤ ህወሃት (ህዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ) ግን ያለ ሊቀመንበር ነበር የሰነበተው። ዛሬ አዲስ አበባ ላይ በተደረገው የህወሃት ስብሰባ፤ አባይ ወልዱ ሊቀመንበር፤ ደብረጽዮን ገብረሚካኤል ደግሞ የህወሃት ምክትል ሊቀመንበር ሆኖ ተመርጧል።
New TPLF leaders: Abay Woldu and Debretsion
አባይ ወልዱ፡ ከቀድሞ ታጋዮች መካከል አንደኛው ነው። በአሁኑ ወቅት የትግራይ ክልል ፕሬዘዳንት እና የህወሃት ምክትል ሊቀመንበር ነበር። መለስ ዜናዊ መታመሙ እንደታወቀም ሆነ፤ ከሞተ በኋላ ሊቀመንበሩን በቀጥታ ተክቶ የህወሃት አባላትን ስብሰባ ጠርቶ ሊቀመንበሩን መተካት ይኖርበት ነበር። ይህንን ባለማድረጉ ባለፈው የኢህአዴግ ስብሰባ ላይ ህወሃት ከሌሎች የዘር ድርጅቶች ይልቅ አንሶ እና ኮስሶ ነበር የታየው። በዚህም ምክንያት ህወሃት በኢህ አዴግ አመራር ውስጥ የነበረውን ይዞታ ማጣቱን የህወሃት አባላት በቁጭት እየተናገሩ ነው። የህወሃት ከፍተኛ ሰዎች ከነበሩት መካከልም፤ አቶ ስብሃት ነጋ… “መለስ ዜናዊ ህወሃትን ገድሎ ነው የሞተው” ሲሉ የሚናገሩትን የሚጋሩ ሰዎች አሉ። እንደ አቶ ስብሃት አነጋገር ከሆነ፤ “ሌሎቹ የኢህአዴግ ድርጅቶች በሰው ሃይል ተጠናክረው ሳለ፤ እኛ ግን ለጠቅላይ ሚንስትርነት የሚበቃ ሰው አላዘጋጀንም። መለስ ዜናዊም በህይወት በነበረበት ወቅት አዋቂ እና የተሻሉ የነበሩትን ሰዎች በሰበብ አስባቡ ሲያባርራቸው ነበር” በማለት እነ ጄነራል ጻድቃን ገብረትንሳይ እና ሌሎችንም ይጠቅሳሉ።

አሁን ዛሬ የተደረገው የህወሃት ስብሰባ ደብረ ጽዮንን ምክትል አድርጎ ከመምረጡ በስተቀር፤ አባይ ወልዱ ሊቀመንበር ሆኖ ሊመረጥ እንደሚችል ቀደም ተብሎም የተጠበቀ ነበር።
አሁን የህወሃት ሊቀመንበር ሆኖ የተመረጠው አባይ ወልዱ በሙስና ውስጥ ብዙም እንዳልተዘፈቀ ይነገራል። በዚህም ምክንያት ሃብት ካካበቱ የህወሃት ሰዎች ጋር ብዙም ወዳጅ አይደለም። ይህ ሁኔታ በሂደት ከቀድሞዋ እመቤት አዜብ መስፍን ጋር ግጭት ውስጥ ሊገባ እንደሚችል ይገመታል። አባይ ወልዱ ከሌሎቹ ይልቅ ጥሩ የመናገር ችሎታ ያለው፤ በህዝብ አስተዳደር እና ጦር አመራር ውስጥ የተሳተፈ፤ በኢሮብ እና በአፋር አካባቢ ያሉ ሰዎች የሚወዱት ግለሰብ ነው። በአፅቢ ዳራ ታጋይ ሆኖ በመቆየቱ፤ በትግል ስሙ አባይ ዳራ ብለው ይጠሩታል። ባለቤቱ ትሩፋት ኪዳነማርያም በማዕከላዊ ኮሚቴ ውስጥ የምትሰራ ሲሆን፤ የደህንነት ሰራተኛ እንደሆነች ይነገራል።
ከዚህ ቀደም በኢ.ኤም.ኤፍ. ትንታኔያችን ላይ እንደገለጽነው… አባይ ወልዱ ከሚታወቅበት ነገር አንዱ ከሁሉም የህወሃት አባላት ጋር ተግባብቶ ለመስራት በሚያደርገው ጥረት ነው። በመሆኑም አሁን መለስ ዜናዊ ባለመኖሩ፤ አሁን ማድረግ ባይችልም ወደፊት ግን በመለስ ዜናዊ ምክንያት ከድርጅቱ ከወጡት… ከነስዬ አብርሃ፣ ገብሩ አስራት፣ አረጋሽ አዳነ፣ ተወልደ ወልደማርያም፣ አለምሰገድ ገብረአምላክ ጋር እንደገና ለመነጋገር እና ለመደራደር ወደኋላ የማይል በመሆኑ ሌሎች የህወሃት ሰዎች በአይነ ቁራኛ የሚያዩት ሰው ነበር። ቢሆንም ግን ከሱ የተሻለ ሰው ባለመገኘቱ ህወሃት ሊቀመንበር አድርጎ መርጦታል። አባይ ወልዱ ከዚህ በኋላ ህወሃት እና ትግራይ ክልልን የበላይ ሃላፊ ሆኖ ይመራል። የግለሰቡ ችግር… ከትልቋ የኢትዮጵያ ጥቅም ይልቅ የህወሃትን ጥቅም የሚያስቀድም መሆኑ ነው። በዚህም ምክንያት መለስ ዜናዊ በፌዴራሉ መንግስት ስራ ውስጥ ተሳታፊ ሳያደርገው መቆየቱ ይነገራል። በቅርብ የሚያውቁት የህወሃት ሰዎች እንደገለጹልን ከሆነ፤ “አባይ ወልዱ ሶስት ነፍስ ቢኖረው፤ ሶስቱንም ህይወቱን ህወሃትን ለማዳን ይጠቀምበታል እንጂ፤ ኢትዮጵያን ለማዳን የሚያጠፋው ትርፍ ህይወት አይኖረውም።” ይህ ትልቅ ችግሩ ነው።
ሌላው የህወሃት ምክትል ሊቀመንበር ሆኖ የተመረጠው ግለሰብ ደብረጽዮን ገብረሚካኤል ነው። በኢትዮጵያ የኮሚዩኒኬሽን እና የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚንስትር፣ ተብሎ በቀድሞው ጠቅላይ ሚንስትር የተሾመ ሲሆን፤ ያለበትን በሙያው አገሪቱን ከማገልገል ይልቅ፤ ሙያውን ለስለላ እና ለመጥፎ አላማ የሚጠቀም ግለሰብ ነው። የአሁኑ የህወሃት ምክትል ሊቀመንበር ደብረጽዮን ገብረሚካዔል፤ በፌዴራል መንግስት ውስጥ በኢትዮጵያ የኮሚዩኒኬሽን እና የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚንስትርነቱን፣ ከስለላ ስራ ጋር ጎን ለጎን የሚያስኬድ በመሆን ከደህንነት ሃላፊው… ሌላኛው የህወሃት አባል ጌታቸው ጋር በቅርበት ይሰራል። ከብአዴን (ብሄረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ) ሰዎች መካከል ከበረከት ስምኦን ጋር ከስራ ውጪ የቀረበ መግባባት አለው። ደብረጽዮን ገብረሚካዔል የኮሚዩኒኬሽን እና የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚንስትር ይባል እንጂ፤ ዋና ስራው የኢህአዴግ ተቃዋሚ የሆኑ ድረ ገጾችን፣ ሬዲዮ እና ቴሌቪዥን ወደ ኢትዮጵያ እንዳይገባ የማገድ ተግባር መፈጸም ሲሆን፤ የግለሰቦችን ኮምፒዩተር እና የስልክ ልውውጦችን መጥለፍ ተጨማሪ የሚንስትርነት ስራው ነው። ደብረጽዮን የሚሰልለው በህዝቡ ዘንድ ያሉትን የኢንተርኔት ግንኙነት ብቻ ሳይሆን፤ ለባለልጣናት የሚሰጡ ኮምፒዩተሮች ጭምር በግለሰቡ ቢሮ የሚስጥር እይታ ውስጥ በመሆናቸው ከፍተኛ ባለስልጣናትን ጭምር በመሰለል፤ የሚያስፈራራና እርምጃ የሚያስወስድ ግለሰብ ነው።
ምናልባት አዲሱ ጠቅላይ ሚንስትርነታቸውን ፓርላማው ያጸድቅላቸዋል ተብሎ ተብለው የሚጠበቁት አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ… እንደ ደብረጽዮን አይነት ሰዎችን በስለላ ሚንስትርነታቸው እንዲቀጥሉ ያደርጓቸዋል ወይስ… ሌላ ለቦታው የሚመጥን ሰው ይሾማሉ? ወደፊት የምናየው ይሆናል። ለዛሬው ግን ህወሃት ሊቀመንበር እና ምክትሉን መምረጡን ለአንባቢዎቻችን አቅርበናል።

No comments:

Post a Comment