Welcome

"The thing that lies at the foundation of positive change, the way I see it, is service to a fellow human being." - Lech Walesa

Sunday 15 July 2012

መንግሥት በኮብልስቶን ሥራ የተሰማሩ ምሩቃን መበረታታት አለባቸው አለ.......ጉድ ነው !!!

Sunday, 15 July 2012 00:00 
“የእኛ ዜጎች ፒኤችዲ ይዘው በአሜሪካ የጥበቃ ሠራተኞች ናቸው” የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር
ዜጎች አንደኛም ይሁን ሁለተኛ ዲግሪያቸውን ይዘው በኮብልስቶን ሥራና በሌሎችም ሥራዎች ላይ ተሰማርተው ከተገኙ፣ መንግሥትም ሆነ ኅብረተሰቡ ማበርታት እንዳለበት የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር ሐምሌ 4 ቀን 2004 ዓ.ም በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ አስታወቀ፡፡
የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስትሩ አቶ መኩሪያ ኃይሌ እንደገለጹት፣ የተማሩ ወገኖች ራዕይ ሰንቀው በሆነ ሥራ ላይ በመሰማራት የአስተሳሰብና የመንፈስ ነፃነት ኖሯቸውና ወደፊት እንደሚቀየሩ አምነው ከሠሩ፣ እነሱን የሚፈታተን ነገር መደረግ እንደሌለበት አሳስበዋል፡፡

ያልተማረን የኅብረተሰብ ክፍል ለተወሰነ ቀናት በማሠልጠን ሊሠራው በሚችለው የኮብልስቶን ጠረባ ሥራ ለ15 እና ለ16 ዓመታት የተማሩ ዜጎችን ማሰማራት “ብክነት አይሆንም?” በማለት የተጠየቁት አቶ መኩሪያ፣ “አንዳንድ ጊዜ በደንብ ማሰብ ይገባናል፤ የእኛ ዜጐች ፒኤችዲ ይዘው በአሜሪካ አገር የጥበቃ ሥራ ይሠራሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ግን ማንም አጀንዳ አድርጎ ያነሳው የለም፤” በማለት በአገራቸውና ለአገራቸው እየሠሩ ነገ የሚቀየሩ መሆናቸውን አስበው፣ አውቀውና ፈልገው ቢሠሩ መደሰት ያለባቸው እንደሚመስላቸው ተናግረዋል፡፡

በአሁኑ ጊዜ ብዙ ዓይነት የሥራ ዕድሎች የተፈጠሩ መሆናቸውን፣ የተወሰነ ሀብት ያለው ቤተሰብ ያላቸው ምሩቃን የተወሰነ ገንዘብ ስለሚያገኙ በተማሩበትና በሠለጠኑበት ሙያ መሰማራት የሚችሉበት ዕድል እንዳላቸው የገለጹት አቶ መኩሪያ፣ የተወሰኑ ምሩቃን ግን ተመርቀው በሚወጡበት ጊዜ ምንም ጥሪት ስለሌላቸው፣ ለተወሰነ ጊዜ በመረጡት ሥራ ላይ ተሰማርተው [ኮብልስቶን መጥረብን ጨምሮ] ጥሪት ከያዙ በኋላ እንደሚለወጡና አገራቸውንም እንደሚጠቅሙ አስታውቀዋል፡፡

በአሁኑ ጊዜ በተለይ በያዝነው የበጀት ዓመት ግዙፍ ግንባታዎችና የተለያዩ ሰፋፊ ፕሮጀክቶች በስፋት እየተሠሩ በመሆናቸው፣ አገርን ከመገንባት አኳያ የተማረውም ያልተማረውም በማንኛውም የሥራ መስክ ተሰማርቶ መሥራት እንዳለበትም አቶ መኩሪያ ገልጸዋል፡፡

ኢትዮጵያ ቀደም ባሉት ዘመናት ስሟ በምን ይጠራ እንደነበርና በአሁኑ ጊዜ ስለሷ ዓለም ምን እያወራ እንደሚገኝ ማንም ዜጋ የሚያውቀው መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሩ፣ “ማንም ኢትዮጵያዊ የሆነ ዜጋ ሁሉ በማንኛውም ሥራ ላይ ቢሰማራ [በኮብልስቶን ጠረባ ላይም ቢሆን] አገሩን እየገነባ መሆኑን አውቀንና የኩራታችን መገለጫ አድርገን መውሰድ ይገባናል፤” በማለት አሳስበዋል፡፡

“የተማረ ሰው የሚሠራበት የሥራ ወሰን የለውም፤ በምርምር፣ በአገልግሎት፣ በቴክኖሎጂ፣ ወዘተ” ሊሰማራ እንደሚችል የገለጹት አቶ መኩሪያ፣ የተማረ ዜጋ የሥራ መስክ እንደጠበበት ተደርጐ መወሳት እንደሌለበትና የተወሰነው በኮብልስቶን፣ የተወሰነው ደግሞ በከተማ ፅዳት፣ የተወሰነው ደግሞ በአረንጓዴ ልማት ሊሰማራ የሚችልበት ሰፊ የሥራ ዕድል መኖሩን ጠቁመዋል፡፡ ይህም በመንግሥት በኩል እንደሚበረታታና ድጋፍ ስለሚደረግለት እንደሚያድግና እንደሚለወጥ ያላቸውን እምነት አክለዋል፡፡

ሚኒስትሩ በመግለጫቸው እንዳስታወቁት፣ በበጀት ዓመቱ መጨረሻ የሥራ አፈጻጸም ለ1‚148 ሺሕ ዜጐች የሥራ ዕድል መፈጠሩንና ከዕቅዱ በላይ የተሳካ ሥራ መሠራቱን ነው፡፡

በዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዱ 3.05 ሚሊዮን ለሚሆኑ ዜጐች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ እንደነበር የተናገሩት ሚኒስትሩ፣ በ2004 በጀት ዓመት ያለው አፈጻጸም ግን 1.15 ሚሊዮን ወይም 189 በመቶ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ይህም በግል ባለሀብቶች የተሰማራውንና በመንግሥት ሲቪል ሰርቪስ መዋቅር የተቀጠረውን እንደማያካትት አረጋግጠዋል፡፡

በአገር አቀፍ ደረጃ የተፈጠረው የሥራ ዕድል በኮንስትራክሽን 237 ሺሕ፣ በአገልግሎት 128 ሺሕ፣ በንግድ 116 ሺሕ፣ በማኑፋክቸሪንግ 107 ሺሕና በከተማ ግብርና 73 ሺሕ መሆኑንም ሚኒስትሩ አስታውቀዋል፡፡ ከዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ፕሮጀክቶች ማለትም ከቤቶች፣ ከመንገድ፣ ከጥርብ ድንጋይ፣ ከኃይል አቅርቦት፣ ከውኃና መስኖ፣ ከባቡርና ከስኳር ፕሮጀክቶች በድምሩ ለ1‚148 ሺሕ ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩን አውስተዋል፡፡ በክልሎችም የተሟላ መረጃ ባይገኝም በኦሮሚያ፣ በአማራ፣ በደቡብ፣ በአዲስ አበባና በትግራይ በድምሩ 66 ሺሕ ለሚሆኑ ዜጐች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡

No comments:

Post a Comment