Welcome

"The thing that lies at the foundation of positive change, the way I see it, is service to a fellow human being." - Lech Walesa

Wednesday 17 October 2012

እኛ “ነጋሲ” ስንልዎ እርስዎ “ሌጋሲ” እያሉ… እየተያየን ተለያየን!? አቤ ቶክቻው


ትላንት ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማሪያም ደሳለኝ (በቅንፍም ቢያንስ ሌላ ጠቅላይ ሚኒስትር በመጥራቴ እኔም ደሳለኝ…!) በፓርላማ ጥያቄዎችን ለመመለስ ለመጀመሪያ ግዜ ቀርበው ነበር። በዚህ የመጀመሪያው የጠቅላይ ሚኒስትሩ ፓርላማ ላይ በርካታ ዋና ዋና የሟቹ ወዳጆች አልተገኙም ነበር አሉ። ወሮ አዜብም ካልተገኙት ውስጥ ናቸው። ወሮዋ ድሮ በሟቹ ጊዜ ስብሰባ ሲቀሩ ከፓርላማው ስብሰባ መልስ ለቀጣዩ መጂሊስ ስብሰባ ቤቱን ሞቅ ሞቅ አድርገው ሊጠብቋቸው ነው የቀሩት ብለን እናስብ ነበር። አሁን ደግሞ ምን ሆነው ቀሩ…? ብለን ስንጠይቅ “ላልተወሰነ ጊዜ ቤተመንግስቱን አምነው ርቀው አይሄዱም አሉ!” የሚል ሽሙጥ እናገኛለን።

የሆነው ሆኖ ግን አቶ ሃይለማሪያም በትላንቱ ፓርላማ መለስን ሆነው ሲተውኑ ነው የተመለከትናቸው። እንደውም አንድ ወዳጄ ሲናገር እንደሰማሁት አፈ ጉባኤው ጠቅላይ ሚኒስትሩን ሲያስተዋውቁ “ቀጥሎ እንደ መለስ ዜናዊ ሆነው እንዲተውኑልን አቶ አርቲስት ሃይለማሪያም ደሳለኝን እጋብዛለሁ!” ማለት ነበረባቸው ብሎኛል።፡

የምር ግን ሰውዬው መለስን ለመምሰል በሚያድርጉት ጥረት ራሳቸውንም መለስንም ሳይሆኑ መቅረታቸው ነው ያሳዘነኝ።

እርግጥ ነው እነ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማሪያም ጊዜ ልንሰጣቸው ይገባል። ሲሉ መክረዋል። የተከበሩ አቶ ግርማ ሰይፉም በዛሬው ፓርላማ ሰውዬው እንዲህ ማድረጋቸው በርካታ የኢህአዴግ አባላትን ያማልልላቸዋል። እናም አማራጭ አልነበራቸውም ብለዋል።

እኔ ግን ያልገባኝ ኢህአዴግ መስተፋቅሩን ያሰራባቸው ግለሰቦች (በቅንፍም መስተፋቅር ተብሎ የተገለፀው አበል እና ሌሎች ጥቅማጥቅሞች መሆናቸው ይታወቅ) እነዚህ ግለሰቦች “ጀግና አይሞትም” ብለው ያሉን እኮ ለለቅሶ ማድመቂያ መስሎኝ ነበር።

የምራቸውን መለስ አልሞቱም ብለው ነው የሚያስቡት እንዴ!? ግራ ነውኮ የሚያጋባው። ትላንት የኢቲቪው ተመስገን አቶ ሃይለማሪያም ቃል በቃል ያሉት ብሎ ስለ አቶ መለስ የተናገረው ነገር በእውነቱ ከሆነ ተስፋ አስቆራጭ ነው።

“የአቶ መለስን “ራዕይ” ማስፈፀም ላይ እና መለስን ዘላለም መዘከር ላይ ድርድር የለም።” “ወ…ይ ድርድር የለም!” ጋዜጠኛው የንግግሩ ዜማ ውስጥ እኮ አሁንም መለስ ይምሩን የሚል ነው የሚመስለው!


የስታድየም ልጆች እስከዚህም የማይደግፉት ክለብ ጨዋታ ላይ ተጫዋቾች የማይሆን አይነት ተደጋጋሚ ስህተት ሲሰሩ ሲያዩ “ምን አገባን እኛ ምን አገባን!” ሲሉ ያዜማሉ… ምክንያቱም ክለቦች እንዲህ ስህተት ከደጋገሙ ከስታድየም የፕሪምየር ሊግ ጨዋታ ዝቅ ብለው ወደ አንደኛ ዲቪዚዮን የጃንሜዳ ጨዋታ ይወርዳሉና የሚመቻቸውን እነርሱ ያውቃሉ ለማለት ነው።

ኢህአዴግ ነብሴ ነብሱ እስክትወጣ መለስ መለስ ብሎ የመለስን መንገድ እከተላለሁ ካለ መጨረሻው ከመሬት ስር ነው። እርሳቸው ያሉት ከመሬት ስርነውና! የምመራው በአስከሬን ነው ያለ ሰው አስከሬን ከመሆን ውጪ ምርጫ የለውም! ለራሳቸው “ባትሪ ሎው” ብለው ለጥ ያሉ ሰውዬ እንደምን ለእኛ ሃይል ይሆናሉ!?

አቶ ሃይለማሪያም ደሳለኝ እኛ ነጋሲ ስንላቸው እርሳቸው “ሌጋሲ” እያሉ እስከመቼ እንደሚቆዩ እንጃ! ሶስቱንም አመት እንዲሁ ከሆኑ “ምናገባን እኛ ምናገባን!” ብለን እናዜምላቸዋለን! ጥሩ ነው እንደውም በሚቀጥለው ምርጫ ኢህአዴግ አንደኛ ዲቪዚዮንን ቢያየው ለልምዱም መልካም ነው!

No comments:

Post a Comment