Welcome

"The thing that lies at the foundation of positive change, the way I see it, is service to a fellow human being." - Lech Walesa

Wednesday 16 May 2012

አፍሪካውያን በኢኮኖሚ የሚያስመዘግቡት ዕድገት የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ እንዳልቻለ የተመድ ጥናት ይፋ አደረገ

  የምግብ ዋስትና ለሰብዓዊ ልማት ቅድመ ሁኔታ ሆኗል

በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም (ዩኤንዲፒ) ጥናት በትናንትናው ዕለት ይፋ ሲደረግ እንዳመለከተው፣ ምንም እንኳ አፍሪካ የኢኮኖሚ ዕድገት የሚመዘገብባት አኅጉር ሆና ብትገኝም በርካታ አፍሪካውያን በምግብ ዋስትና ችግር ምክንያት ለከፋ ረሃብና ለተመጣጠነ ምግብ እጦት ይዳረጋሉ፡፡
በአፍሪካ ተገቢውን የተመጣጠነ ምግብ ማግኘት የማይችሉ ሕፃናት ቁጥር 55 ሚሊዮን ገደማ ሲደርስ፣ ይህም ከአሥር ዓመት በፊት ከነበረው ከፍተኛ መጠን እንደሆነና ይበልጥ እየጨመረ እንደሚሄድም የሚጠበቅ ነው፡፡ እንደ ሪፖርቱ፣ ባለፉት አሥር ዓመታት የተመጣጠነ ምግብ ዕጦት የሚያሰቃያቸው ሕፃናት ቁጥር የቀነሰው በአንድ በመቶ ብቻ ሲሆን፣ በአንጻሩ እስያ ያሉ አገሮች ውስጥ ከፍተኛ መሻሻል ተመዝገቧል፡፡ በመላ አፍሪካ ከሚኖሩ ሰዎች ከአራቱ አንዱ ወይም 218 ሚሊዮኑ ተገቢውን የምግብ መጠን አያገኙም፡፡

በአፍሪካ የግብርና ዘርፍን በተመከለተ የሰብዓዊ ልማት ሪፖርቱ እንዳመለከተው፣ ምንም እንኳ አፍሪካ በርካታ ወንዞችና የውኃ ምንጮች ቢኖሯት 93 በመቶ የሚሆነው ለእርሻ ተስማሚ መሬቷ የዝናብ ጥገኛ ነው፡፡ ገበሬዎቿም በሔክታር ለእርሻ የሚያውሉት ማዳበርያ ከ20 ኪሎ የማይበልጥ፣ በአንጻሩ እስያውያን እስከ 350 ኪሎ ግራም እንደሚጠቀሙ በጥናት መረጋገጡንና ስለሆነም አፍሪካውያኑ ለዝቅተኛ ምርታማነታቸው አንዱ መንስዔ እንደሆነባቸው ይገልጻል፡፡

በአፍሪካ በየዓመቱ ከሚመዘገበው የኢኮኖሚ ዕድገት በተጻራሪ መልኩ የምግብ ዋስትናና የድርቅ እንዲሁም የረሃብ ችግሮች ከፍተኛ ጫና ያሳደሩ መሆናቸው ሲገለጽ፣ ለመጀመርያ ጊዜ ይፋ በተደረገው ይህ የአፍሪካ ሰብዓዊ ልማት ሪፖርትም የመጪው ጊዜ የምግብ ዋስትና ለአፍሪካ ወሳኝ የፖሊሲ ጥያቄ መሆኑን እንደሚያመለክት የተመድ የልማት ፕሮግራም ኢኮኖሚ ጉዳዮች አማካሪ ሳሙኤል ብዋሊያ ለሪፖርተር አብራርተዋል፡፡

በአፍሪካ ለሰብዓዊ ልማት (የትምህርት፣ የጤና፣ የመሠረተ ልማትና የመሳሰሉት… አገልግሎቶችን በቀላሉ ማግኘት መቻል) መሠረታዊ ችግሮች ከሆኑት መካከል ግንባር ቀደም የሆነው የምግብ ዋስትና አለመረጋገጥ መሆኑን የጠቀሱት ብዋሊያ፣ ይህንን ችግር መቅረፍ መቻል የሰብዓዊ ልማቱን ዕድገት እንደሚያሻሽለው ገልጸዋል፡፡

ያም ሆኖ የመሠረተ ልማቶች አለመሟላትም እንደ አንድ ችግር የሚጠቀስ ሆኖ በአፍሪካ  የገጠሩ ሕዝብ ወደ ዋና መንገድ ለመውጣት በሁለት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚኖረው ሕዝብ ከ30 በመቶ የማይበልጥ ነው፡፡ በደቡብ እስያ ሁለት ኪሎ ሜትር ከዋና መንገድ ርቀው የሚኖሩት 58 በመቶ ያህሉ ናቸው፡፡ ይህም አብዛኛው የገጠሩ ሕዝባቸው ለመንገድ አቅራቢያ ሆኖ እንደሚኖር ያመለክታል፡፡

አፍሪካውያን ለምግብ ዋስትና ችግር የተጋለጡት መንግሥታቱ እንደሚገባቸው መጠን በግብርና ዘርፍ ላይ ኢንቨስትመንት ባለማካሄዳቸው ሳቢያና ትኩረት በመንፈጋቸው ምክንያት ድርቅና ረሃብ በርካቶችን እንደሚያሰቃይ ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡ ከአሥር ዓመት በፊት ሁሉም የአፍሪካ አገሮች ያፀደቁትና ሁሉን አቀፍ የአፍሪካ የግብርና ልማት ፕሮግራም እንደሚያትተው፣ አገሮቹ የኢኮኖሚያቸውን አሥር በመቶ ለግብርና እንዲያውሉ የተስማሙበት ቢሆንም፣ ሁሉም አገሮች ያንን እየተገበሩ እንዳልሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት በተካሄደ ጥናት ጥያቄ ከቀረበላቸው ውስጥ ስድሳ በመቶ ያህል የአፍሪካ መሪዎች በምግብ ዋስትና ዙርያ ተገቢውን እያከናወኑ ናቸው የሚል እምነት እንደሌላቸው ሪፖርቱ ይጠቅሳል፡፡

ከሰሐራ በታች ያሉ አገሮች ባለፉት አሥር ዓመታት አማካይ የዝናብ መጠን በከፍተኛ መጠን ቀንሶ የታየባቸው ናቸው፡፡ በድርቅ የተመቱ፣ በከፍተኛ ሙቀት መጨመርና በሰደድ እሳት ምክንያት የሚሰቃዩ ሰዎች ቁጥር በእጥፍ የጨመሩባቸው ሕዝቦች ቢኖሩ እነዚህ የአፍሪካ ክፍል ሕዝቦች በመሆናቸው በአኅጉሪቱ እየተመዘገበ ነው የተባለለት የኢኮኖሚ ዕድገት ወደ ታች ወርዶ ሕዝቦችን ሁሉ ተጠቃሚ እንዳላደረገ በተግባር የታየበት፣ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ አገሮችም ምንም እንኳ የኢኮኖሚ ዕድገታቸው እንደሚቀጥል ቢረጋገጥ የምግብ ዋስትናንም ሆነ መሠረታዊ የተፈጥሮ ክስተት አደጋዎችን ለመከላከል ያልቻሉበት፣ ሁሉንም ሕዝብ የኢኮኖሚ ዕድገታቸው እኩል ተጠቃሚ ማድረግ ያልቻሉበት ዕድገት በመሆኑ የፖሊሲ አቅጣጫቸውን ዳግም እንዲመለከቱ የሚያመላክት ሪፖርት ይፋ መሆኑን አፍሪካ ኅብረት ምክትል ሊቀ መንበር የሆኑትን ኤራስተስ ምዌንካን ጨምሮ በርካቶች የተስማሙበት ነው፡፡

ሪፖርቱ በጠቅላላው እንደሚያመለክተው፣ በአፍሪካ የምግብ እጥረት ችግርን ለመቅረፍ ያን ያህል የሚያመረቃ ሥራም ሆነ ውጤት እንደማይታይ ነው፡፡ በአንጻሩ ላለፉት አሥር ዓመታት በአፍሪካ የተመዘገበው የኢኮኖሚ ዕድገት፣ አሁንም የሚታየው የኢኮኖሚ ኡደት ይህንን የምግብ ችግር የሚቃረን እንደሆነ የገለጹትና ሪፖርቱን በይፋ የመረቁት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ናቸው፡፡ አቶ ኃይለ ማርያም እንዳመለከቱት፣ ምግብ በተትረፈረፈበት ዓለም ከሰሐራ በታች ያለው የአፍሪካ ክፍል በምግብ እጦትና በረሃብ ችግር ውስጥ ይገኛል፡፡

የአፍሪካ ቀንድ አገሮች በአምናው ድርቅ ሳቢያ ለማገገም በሚታገሉበት ወቅት ሪፖርቱ መውጣቱ አስፈላጊና ወቅታዊ ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በረሃብና ችጋር ምክንያት ከሰሐራ በታች በሚገኙ አገሮች ላይ የሚደርሰው ጫና እየቀጠለ እንደሚገኝና ከእነዚህ ችግሮች በሻገር ግን ሥር ሰደደ ድኅነት፣ የተደራጀ ወንጀል፣ ሙስና፣ ሕገወጥ ሰዎች ዝውውርና የመሳሰሉት በአፍሪካ አዳዲስ ክስተቶች ሆነው የሰብዓዊ ልማትን እንደሚፈታተኑ ተናግረዋል፡፡

በጤና አኳያም ምግብ ዋስትናን ያህል አይሁን እንጂ ከፍተኛ ችግሮች ከሰሐራ በታች ባሉ የአፍሪካ አገሮች እንደሚታይ የሚጠቁመው ሪፖርቱ፣ አንድ የሕክምና ዶክተር ከ5,300 በላይ ሰዎችን በአማካይ ለማከም እንደሚገደድ፣ በአንዳንድ አገሮች ይህ መጠን በ50 ሺሕ ድረስ እንደሚዘልቅ ሪፖርቱ ይፋ አድርጓል፡፡ ከእነዚህ አገሮች አንዷ ኢትዮጵያ ሆና ትገኛለች፡፡

በ40 በመቶ የማያንሱ አፍሪካውያን ንጹህ የመጠጥ ውኃ የማግኘት ዕድል የላቸውም፡፡ 31 በመቶ የሚሆኑት ብቻ በአንጻራዊነት የተሻሻለ የሳኒቴሽን አገልግሎት ያገኛሉ፡፡ ይህ በማደግ ላይ ከሚገኙ አገሮች አንጻር (በአማካይ ዝቅተኛው 53 በመቶ ነው) እጅግ ዝቅተኛውና ለጤና ቀውስ ከሚያጋልጡ ምክንያቶች አንዱ ሆኖ የተመዘገበው ነው፡፡

ከሰባ በመቶ ያላነሱ ቤተሰቦች በአፍሪካ የኤሌክትሪክ ኃይል አያገኙም፡፡ በመሆኑም በከፍተኛ መጠን ለማገዶና መሰል የኃይል ምንጮች ጥገኛ ናቸው፡፡ እነዚህ ቤተሰቦች የቫይታሚንና የአዮዲን እጥረት በከፍተኛ መጠን የሚታይባቸው ሆነው ይገኛሉ፡፡

ሪፖርቱ በአፍሪካ የምግብ ዋስትና ጉዳዮች ላይ እንዲያጠነጥንና ለብቻው እንዲዘጋጅ የሆነበት ምክንያትም የአፍሪካ ጉዳይ ከተቀረው ዓለም የሰብዓዊ ልማት ጉዳይ ለየት ያለበት ሁኔታ በመኖሩ ነው ያሉት ብዋሊያ፣ ከዓለም የሰብዓዊ ልማት ጠቋሚ አሃዞች አኳያ አፍሪካ ያላትን ደረጃ የምታሻሽልበትን መፍትሔ ለመጠቆም አማራጩ በተለየ ሁኔታ የአፍሪካ ጉዳይ ላይ ብቻ ያተኮረ የጥናት ሪፖርት ማዘጋጀቱ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

በተባበሩት መንግሥታት የልማት ፕሮግራም ተወካይ የሆኑት ኤውጄኔ ኦውሱ እንዳስታወቁት፣ የሰብዓዊ ልማት ሪፖርቶች መዘጋጀት የጀመሩት እ.ኤ.አ. በ1990 ሲሆን፣ ከዚያን ጊዜ ወዲህ 22 ዓለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ፣ 670 ደግሞ በእያንዳንዱ አገር ላይ ያነጣጠሩ ሪፖርቶች ይፋ ተደርገዋል፡፡

በዓረብ አገሮች ነፃነት ላይ ያጠነጠነው የመጀመርያው የፕሮግራሙን ሪፖርት ተከትሎ ለመጀመርያ ጊዜ ይፋ የሆነው የአፍሪካ ሰብዓዊ ልማት ሪፖርት እንደ አንዳንዶች ተሳታፊዎች አስተያየት እጅግ ቢዘገይም፣ ሪፖርቱ ይፋ መሆኑ ግን ከምንም ይሻላል ባይ ናቸው፡፡

ይህንን ተቋም በአፍሪካ ቢሮው ደረጃ በዳይሬክተርነት የሚመሩት አቶ ተገኘወርቅ ጌቱ እንደተናገሩት፣ አፍሪካ የምግብ ልመና ማቆም አለባት፡፡ ካላት አቅምም ሆነ ከክብሯ አኳያ የምግብ ልመና ማቆም ይገባታል ያሉት ተገኘወርቅ፣ አንዳንድ የአፍሪካ አገሮች ተዋጊ ጄቶችን፣ የጦር መሣርያዎችንና ሌሎችም የተራቀቁ የጥፋት ቁሳቁሶችን ገንዘባቸው ማድረግና ማሠራጨትን ከቻሉ አፍሪካ ለምን የግብርና ዕውቀት ባለቤት እንደማትሆን በማሳሰብ ጥያቄያቸውን ያቀርባሉ፡፡ ለምንስ አፍሪካውያን ለምግብ ዋስትና መሠረት የሆነውን የመስኖ፣ የትራክተር፣ የተሻሻለ ዘርና ሌላውንም ቴክኖሎጂ ለማግኘት እንዴት እንደሚሳናቸው ይጠይቃሉ፡፡

የአፍሪካውያን የምግብ ዋስትና ቢረጋገጥ የኑሮ ደረጃው ተሻሽሎ ለነገ ልጆቻቸውና ለልጅ ልጆቻቸው የሚያወርሷት አኅጉር ይበልጥ የተመቻቸችና ብልጽግና የተላበሰች እንደምትሆን ተስፋ ቢደረግም፣ በተግባር የየአገሮቹ የኢኮኖሚ ዕድገት የሚያመለክተው ግን ከስታቲስቲክስ ውጤቶች ከሚገለጸው በእጅጉ የተጻረረ በመሆኑ፣ ተግባራዊ ለውጥ ለማምጣት ሁሉም አገሮች ቃል የገቡትን ሁሉ በተግባር እንዲተገብሩት ጥሪ ቀርቧል፡፡

No comments:

Post a Comment