Welcome

"The thing that lies at the foundation of positive change, the way I see it, is service to a fellow human being." - Lech Walesa

Monday 20 August 2012

አላማችን ላይ ሊያደርሱን ያልቻሉ መጣመሮች


ከጌዲዮን ደሳለኝ (ኖርዌይ)
ወደድንም ጠላንም የኢትዮጵያ ሁኔታ ወደአንድ አቅጣጫ እያመራ እንደሆነ እየተከናወነ ያለው እውነታ ይመሰክራል ነገሮች በፍጥነት እየተለወጡ ነው ያለው፣ ትላንት የሰማነውን አዲስ ነገር አጣጥመን ሳንጨርስ ሌላ አዲስ ነገር ይፈጠራል ይህ ደግሞ በአገራችን እየተከናወነ ያለ የለት እለት ክስተት ሆኗል።
የዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነኝ ዋናው ምክንያት እኛ ስንጣመር፤ ስንቀናጅና ስንተባበር ትግሉን በዚህ ብቻ በመጨረስ። የተግባር መግቢያው ወቅት እያለፈን እንዳለ ስለተገነዘብኩ ነው። አንዳንዴ እንደውም እኛ ተቃዋሚ የምንባለው የወያኔ ስርአት ተወደቀ የምንጎዳ ይመስል ወደትግል ከመግባትና ከማስገባት፣ ከመታገልና ከማታገል ይልቅ ስንተባበር፣ ስንቀናጅና ስንጣመር ዘመናትን ያስቆጠርን ይመስላል በዚህም ወሳኝ የሆኑ የለውጥ ወቅቶች እያለፉን ይገኛሉ።

ጀግናው የተወደደ አበበ ገላው አቶ መለስ ላይ የኢትዮጵያውያንን ቁጣ ካወረደባቸው በኻላ በደረሰባቸው ታላቅ መቅሰፍት ይኽው ከመድረክ ከጠፉ ሁለት ወራቶች ተቆጠሩ በጀግናው አበበ ገላው የተለኮሰው እሳት ከሳቸው መጥፋት ጋር ተዳምሮ በኢትዮጵያውያን ዘንድ ተስፋ የሚሰጥ እንቅስቃሴዎች ተጀምረው ነበር አገሬውም ውጭ ያለውም ብሩህ ዘመንን እያየ ለለውጥ ሲነጋገር፣ ሲሰራና ቢንቀሳቀስም ማንም ከጎኑ ቆሞ የሚረዳውና ትግሉን የሚመራለት አካል አላገኘም።
መተባበር፤ መቀናጀትና መጣመር ለትግን ጠቃሚ መሳሪያ እንደሆነ ማንም አይዘነጋውም ነገር ግን ከዚህ በማያያዝም እንደሚባለው መሬት የረገጠ ትግል ስናደርግ ነው እንድምታ፣ ጥቅምና ውጤት የሚኖራው እንጂ ትርጉም የሌለው መተባበር፤ መቀናጀትና መጣመር ወያኔን ግዜ እንዲገዛ ከማድረግና ለሱ እስትንፋስ ከመስጠት በስተቀር የሚፈይደው ፋይዳ የለም።
ስለለውጥ የሚሰብኩና የሚዘምሩ ተቃዋሚዎችና ህብረቶች የሚፈተኑበት ሰአት አሁን ነው። ህዝብ ምሩን፣ አታግሉን፣ ለድል አብቁን፣ ቀንበሩን ከላያችን ላይ አንከባሉልን፣ ከግፍ ከእስራትና ከእንግልት አድኑን እያለ በሚጣራና በሚጮህ ሰአት ተቃቃሚዎች ትላንት ስንጣመር፣ ዛሬም ስንተባበር፣ ነገም ስንቀናጅ በእጃችን ላይ ያሉ ያለቀላቸው የድል ወቅቶች እያመለጡን ይገኛሉ።
መች ጠባችን ከመተባበር፤ ከመቀናጀትና ከመጣመር ጋር ሆነና፣ ጠባችን ከዛወዲያ የት አላችሁ? ከሚለው ጋር ነው እንጂ። ተገናኙ፤ ተነጋገሩ፤ ተጨባበጡ ስንባል እሰይ እልል እንደምንል ሁሉ ከዛ በኻላ ድምጻችሁ ሲጠፋ የደረሳችሁበት ሳናውቅ ስንቀር ወቅቱ እንዳያመልጠን ስለምንሰጋ እንጨነቃለን። ለለውጥ ከዚህ የበለጠና የተመቸ ጊዜ መቼም ሊመጣ እንደማይችል ለመገመት ጠበብት መሆን አያስፈልግም፤ በዚያች አገር የሆነ ነገር ሊወለድ እንዳለ ምልክቶች እየታዩ ነው ግን ጥያቄው አዋላጅ ከየት ይምጣ ነው? ከሌለ ደግሞ የሚወለደው ሊጨነግፍ ይችላል።
ለህብረት፣ ለመጣመር እና ለመቀንቅጀት እንደምንሯሯጥ ሁሉ ትግሉን ከግብ ለማድረስ ምነው ሰነፍን ጎበዝ ይህ ወቅትም እየሮጠ እንደሆነ መገንዘብ አለብን ወያኔ የተንገዳገደውንና የተሰነጠጠቀውን ያህል ተባብረን በአፋጣኝ ግዜ ሳንሰጥ ገፍተን ካልጣልነው በሚያገኘው ትንሽም ግዜና ትንፋሽም ቢሆን ነፍስ ዘርቶና አንሰራርቶ
ጭንቅላታችን ላይ ሊቆም ስለሚችል ልንፈጥንና ወደስራ ልንገባና ልናስገባ ያለው ሁኔታ የግድ ይላል።
በመሆኑም ወቅቱ የስራ መሆኑን ተገንዝበን የተባበራችሁ አካላት ሁሉ ለውጥ ፈላጊውን ማህበረሰብ በማስተባበርና በማቀናጀት መሬት ወደረገጠው ትግል ግዜ ሳንወስድ እንድንገባና የወያኔ አገዛዝን እድሜ እንድናሳጠር ወቅታዊውን የህዝብ ጥያቄ ታደምጡ ዘንድ ታሪክና ወቅቱ ያስገድዳል።
ስለዚህ ለተከበራችሁ፣ የተባበራችሁ፣ የተቀናጃችሁ እንዲሁም የተጣመራችሁ አካላት በሙሉ ይህ ጥሪያችን አክብራችሁ ትግሉ በሚጠይቀው በአሁኒቷ ወሳኝ ሰአት እኛን በማስተባበር በመምራት ለድል ታበቁን ዘንድ ጥሪያችንን እናቀርባለን።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!

No comments:

Post a Comment