Welcome

"The thing that lies at the foundation of positive change, the way I see it, is service to a fellow human being." - Lech Walesa

Wednesday 23 May 2012

በጋምቤላና በቤንሻንጉል የፀጥታና የማስፈጸም ችግሮች ለፕሮጀክቶች እንቅፋት ሆነዋል

Wednesday, 23 May 2012 09:48
By Wudineh Zenebe

በአቶ አዲሱ ለገሰ የሚመራው የፌዴራል መንግሥት ልዑካን ቡድን በጋምቤላና በቤንሻንጉል ጉምዝ ክልሎች ባካሄደው የመስክ ግምገማ፣ የመንደር ማሰባሰብ ሥራዎች ችግር እየገጠማቸው መሆኑን አረጋገጠ፡፡ 
አቶ አዲሱና የቀድሞ የትግራይ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ፀጋዬ በርኸ የሚገኙበት የልዑካን ቡድን ካለፈው ማክሰኞ ጀምሮ እስከ ቅዳሜ ድረስ በሁለቱ ክልሎች ስብሰባዎችንና የመስክ ጉብኝቶችን አካሂዶ ባለፈው እሑድ ተመልሷል፡፡

በዚህ ወቅት በቤንሻንጉል ክልል በዋናነት ፕሮጀክቶችን በማስፈጸም በኩል ደካማ የሥራ አፈጻጸም ሲያሳይ፣ በጋምቤላ ክልል ደግሞ ቀደም ሲል የተፈጠረው የፀጥታ መደፍረስ ፕሮጀክቶች የተፈለገውን ያህል መራመድ እንዳይቻሉ ማድረጉ ተጠቅሷል፡፡

የፌዴራል መንግሥት በ2004 ዓ.ም. የምዕተ ዓመቱን የልማት ግቦች እንዲሳኩ ለማድረግ ለሁሉም  ለክልሎች የሚከፋፈል 15 ቢሊዮን ብር መድቧል፡፡ የቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ከዚህ ገንዘብ ውስጥ 294 ሚሊዮን ብር ሲደርሰው፣ በዚህ ገንዘብ በዋናነት ተበታትነው የሚገኙ የክልሉን ነዋሪዎች በመንደር ማሰባሰብ፣ ውኃ፣ ጤናና የትምህርት ተቋማትን የማሟላት ሥራ የመሥራት ዕቅድ ተይዟል፡፡ ነገር ግን የበጀት ዓመቱ ሊጠናቀቅ አንድ ወር ብቻ እየቀረው ክልሉ ከዚህ ገንዘብ ውስጥ የተጠቀመው ከ30 በመቶ እንደማይበልጥ ምንጮች ገልጸዋል፡፡

የልዑካን ቡድኑ ባምባሲ አካባቢ በሚገኘው በጀማፃና በጋሪቡ መተማ አካባቢ የሚካሄደውን የመንደር መሰባሰብና የመስኖ ፕሮጀክቶች ከጎበኘ በኋላ የሥራ አፈጻጸሙ ዝቅተኛ መሆኑን ደምድሟል፡፡

የክልሉን ፕሬዚዳንት አቶ አህመድ ናስርን ጨምሮ የክልሉ ሴክተር መሥርያ ቤቶች በተገኙበት በአሶሳ ከተማ በተካሄደው ስብሰባ ክልሉ ደካማ አፈጻጸም ማሳየቱ ተገልጿል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በዕድገት ወደኋላ የቀሩ ክልሎችን እንዲደግፉ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ትዕዛዝ የተሰጣቸው የትምህርት ሚኒስቴር፣ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር፣ የውኃና ኢነርጂ ሚኒስቴር መሥርያ ቤቶች የሚጠበቅባቸውን ድጋፍ እንዳልሰጡ መጠቆሙን መረዳት ተችሏል፡፡ በዚህ ስብሰባ በሚቀጥሉት ሁለት ወራት ያለፉት ስህተቶች ታርመውና ሥራው ተካክሶ እንዲሠራ መመርያ ተሰጥቷል፡፡

በጋምቤላ ክልል ኦደግሞ የኦቦቦ መንደር ማሰባሰብና የላሬ ወረዳ መንደር ማሰባሰብ ሥራዎች ተጎብኝተዋል፡፡ በእነዚህ ጣቢያዎች የማስፈጸም አቅም ማነስ ቢኖርም፣ ለሥራው አፈጻጸም ዝቅተኛ መሆን ዋነኛው ተጠቃሽ ምክንያት የሆነው በ2004 ዓ.ም. በክልሉ ውስጥ የተፈጸሙ ሁለት ግድያዎች ናቸው፡፡ በርካታ ሰዎች ያለቁባቸው እነዚህ ግድያዎች የክልሉ አስፈጻሚ መሥርያ ቤቶች በሚፈልጉት ፍጥነት ሥራቸው ላይ እንዳያተኩሩ አድርገዋል ተብሏል፡፡

“የፀጥታ መደፍረስ አጋጥሟል” ሲሉ የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ጋት ሉዎክ የሥራ አፈጻጸሙ ዝቅተኛ የሆነበትን ምክንያት ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ የፀጥታ ችግር በማጋጠሙ የክልሉ ባለሥልጣናት አብዛኛው ጊዜያቸውን በዚሁ ጉዳይ ላይ አጥፍተዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ክልሉ በጠየቀው መሠረት የፌዴራል መንግሥት ዘርፈ ብዙ ድጋፍ እያደረገ መሆኑን አቶ ጋት ሉዎክ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

መንግሥት በ2007 ዓ.ም. የሚጠናቀቀውን የምዕተ ዓመቱን የልማት ግቦችን ለማሳካት ዕቅድ መንደፉ ይታወሳል፡፡ ዕቅዱን ለማስፈጸም ከተያዙ አቅጣጫዎች መካከል በዕድገት ወደኋላ የቀሩ ክልሎች መሠረት ልማትን ለማሟላት አመቺ ባለመሆኑ ነዋሪዎች ተሰባስበው በመንደር እንዲቋቋሙ ማድረግ አማራጭ ሆኗል፡፡ በዚህም ውኃ፣ ትምህርት፣ ጤናና የመንገድ መሠረተ ልማት ማሟላት ይጠበቅበታል፡፡

አቶ አዲሱ በዕድገት ወደኋላ የቀሩ ክልሎችን ለመደገፍ የተቋቋመውን ቦርድ የሚመሩ ሲሆን፣ አቶ ፀጋዬ ደግሞ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የደኅንነት ጉዳዮች አማካሪ ናቸው፡፡

No comments:

Post a Comment