Welcome

"The thing that lies at the foundation of positive change, the way I see it, is service to a fellow human being." - Lech Walesa

Saturday 12 May 2012

በውጭ የሚገኘው ሲኖዶስ በሙስሊሞች ላይ የተፈጸመውን ግድያ አወገዘ

ግንቦት ፬ (አራት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በስደት የሚገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቅዱስ ሲናዶስ፤  በአርሲ-አሰሳ የመብት ጥያቄ ባነሱ ሙስሊሞች ላይ የኢህአዴግ ታጣቂዎች  ተኩስ በመክፈት  የፈፀሙትን ግድያ አጥብቆ አወግዟል።
ሲኖዶሱ  በኢትዮጵያ ሙስሊሞች ላይ የተፈፀመውን ግድያ እና አሁንም እየተፈፀመ ያለውን  በደል ያወገዘው ሰሞኑን ያካሄደውን 33 ኛ ጉባኤውን ሲያጠናቅቅ ባወጣው የአቋም መግለጫ ነው።
ሲኖዶሱ በዚሁ የአቋም መግለጫው በአሰሳ-መስጊድ የተፈፀመውን ግድያ ከማውገዝ በተጨማሪ፤ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ህገ-መንግስቱ በፈቀደላቸው መሰረት  ሀይማኖታቸውን በነፃነት እንዳይከተሉ መንግስት ጣልቃ እየገባ በተለያዬ መንገድ ከሚያደርግባቸው ጫና በአስቸኳይ እንዲቆጠብ ጠይቋል።
ሀይማኖታዊ መብትን ከማስከበር እንቅስቃሴው ጋር ተያይዞ የታሰሩት ሙስሊም ወንድሞችና እህቶችም ፤ በቶሎ እንዲፈቱ ሲኖዶሱ አሣስቧል።
ክርስቲያኖች እና ሙስሊሞች ተዋደው እና ተከባብረው ከሚኖሩባቸው የዓለማችን አገሮች ኢትዮጵያ በግንባር ቀደምነት የምትጠቀስ እንደሆነች መረጃዎች ያሳያሉ።
ድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን- በቅጽል ስሙ ቴዲ አፍሮ በምርጫ 97 ዋዜማ ባሰማው “ሸመንደፈር”የተሰኘ ሙዚቃው፦
“ሸገር አዲሳባ-አንች ያለሽበቱ፣
ራጉኤል አይደል ወይ-የአንዋር ጎረቤቱ፣
ቅዳሴ እና አዛኑን-አጥር ቢለያቸው፣
ፈጣሪ ከሰማይ-ባ’ንድነት ሰማቸው” በማለት፤ በኢትዮጵያ በሁለቱ እምነት ተከታዮች ዘንድ ያለውን ተከባብሮ እና ተዋዶ የመኖር ታሪክ እና እውነታ ይታወሳል።
ህዝባዊ ተቀባይነቱ በመሟጠጡ ከፍ ያለ ፖለቲካዊ ኪሳራ ውስጥ የሚገኘው ገዥው ፓርቲ፤ በተለይ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የሁለቱን እምነት ተከታዮች ለማጋጨት፣  በጥርጣሬ ለማስተያዬት እና በዚህም ህዝቡ በአገራዊ ጉዳዮች ላይ አንድ ላይ እንዳይቆም ለማድረግ በተደጋጋሚ አደገኛ ቅስቀሳዎችን ሲያደርግ መቆየቱን ብዙዎች ይናገራሉ።
በቅርቡ ብዙሀን ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች መብታቸውን ለማስከበር እንቅስቃሴ መጀመራቸውን ተከትሎ ፦አንድ ጊዜ “አክራሪዎችና አሸባሪዎች እየተስፋፉ ነው”  በማለት የነዛው ፕሮፓጋንዳ ህዝባዊ ተቀባይነት ሊያገኝለት እንዳልቻለ የተገነዘበው ኢህአዴግ፤ ከሰሞኑ ደግሞ ተቃውሞ ያሰሙትን ሙስሊሞች፦ “ሀሳባቸው የሸሪአ መንግስት ለማቋቋም ነው”በማለት በሌሎች እምነት ተከታዮች ዘንድ በጥርጣሬና በፍርሀት እንዲታዩ ቅስቀሳ መጀመሩ ይታወቃል።
የብዙሀኑ ሙስሊም አስተባባሪ ኮሚቴ ፦”በሀሰት ፕሮፓጋንዳ የመብት ጥያቄን ማዳፈን አይቻልም” በሚል ርዕስ ሰሞኑን  በበተነው ወረቀት ፤ መንግስት የዚህ ዓይነት ቅስቀሳ የጀመረው ፤የሙስሊሞች መብት የማስከበር እንቅስቃሴ በክርስቲያን ወንድሞቻቸው ዘንድ በጥርጣሬ እንዲታይና ድጋፍ እንዳያገኝ ለማድረግ መሆኑን በመጥቀስ፤ ከዚህ አይነት አደገኛ የውሸት ቅስቀሳ እንዲቆጠብ ማሣሰቡ አይዘነጋም።
የብዙሀኑን ሙስሊም አስተባባሪ ኮሚቴ እና በስደት የሚገኘው ሲኖዶስ ያወጧቸውን መግለጫዎች የተመለከቱ አንድ አባት፦” በሁለቱም ወገን የወጡት መግለጫዎች ፤መንግስት ተከባብረውና ተዋደው የኖሩትን ህዝቦች በእምነት ምክንያት ለማናቆር እና ለማጋጨት ለዓመታት ቢደክምም፤ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች እና ክርስቲያኖች  አንድኛቸው ለሌላው ያላቸው አክብሮት እና አስተሣሰብ ዛሬም እንደ ጥንቱ በፍቅር ላይ የተመሰረተ እንደሆነ  የሚያመለክቱ ናቸው”ብለዋል።

No comments:

Post a Comment