Welcome

"The thing that lies at the foundation of positive change, the way I see it, is service to a fellow human being." - Lech Walesa

Wednesday 30 May 2012

ያለ ጨረታ ! ለነ ሌንጮ ለታ ? እንግዳ/ ከኦስሎ

May 29th, 2012 

’’የመለስና የሌንጮ የመግባባትና የስምምነታቸው መሰረት ከቶ ምን ሊሆን ይችላል? የድርድራቸው ማእከልና ያግባባቸው የጋራ ፍላጎት ምንድነው? አልገባኝም። መረጃም የለኝም። ማለት የሚቻል ነገር ግን ይኖራል። ሌንጮና ዲማ የዋህ ፖለቲከኞች አይደሉም። ’’የአበሻን ተንኮል አሳምረው የሚረዱ ናቸው ’’። ያግባባቸው አንድ የጋራ የሆነ ማእከላዊ ነጥብ ግን የግድ ይኖራል። ’’ተስፋዬ ገ/ አብ
መቸም ! ተስፋየ በጥሩ ብዕሩ እያዋዛ በሚለቃቸው መጣጥፎቹ ውስጥ በየመስመሮቹ መሃል ወሸቅ የሚያደርጋቸው አፋጀሽኝ ቃላቶቹ አሁንም አልለቀቁትም ፡፡ ’’ ያደቆነ ሰይጣን ሳያቀስ አይለቅም ’’ ሆነና አድባር ስትከፍትለ’ት በሚለቃቸው መጣጥፎቹ መስመሮች ውስጥ – በአብዛኛው በአማራና – ኦሮሞ ህዝብ ውስጥ ንትርክ እንዲቀጥል ሲፈልግ ፣ ዛሬ ደግሞ ሴሜቲኮችና ኩሺትኮች በሚላቸው ኢትዮጵያውያን መሃል ሽኩቻው እንዳያባራ – የአበሻን – ተንኮል አሳምረው ሌንጮና ዲማ ያውቁታል በሚል ጥርጣሬው እንዲጠጥር በር ይከፍታል፡፡ ይህች አንጓ አስታራቂ ናት ወይስ ቀጣይ ጥርጣሬን ጫሪ ? ደራሲ ተስፋዬ ?
ካልተሳሳትኩ ተስፋዬ በአንድ ጽሁፉ ላይ ከኦቦ ሌንጮ ለታ ጋር ጥብቅ የሆነ ወዳጅነት እንደነበረው ፣ ኔዘርላንድ በአንድ ወቅት አብረው እንደከረሙና ፣ በቀጣይነትም ኦቦ ሌንጮ ከሚገኙበት ስካንዲኔቪያዋ አገር ኦስሎ መጥቶ እንደሚጎበኛቸው በጽሁፉ አስነብቦን ነበር ፡፡ ይህ የሚያሳየው የወዳጅነታቸውን ጥብቅ ትሥሥር ሲሆን ፣ የቤተ መንግሥቷን ሹክሹክታ እንዳለ ሙሉ በሙሉ ባይነግሩትም በገደምዳሜ ግን ቅርፊት ቅርፊቷን እንዴት እንዳልነገሩት አልገባኝም፡፡ የድርድራቸው ማዕከልና ያግባባቸው የጋራ ፍላጎት ምንድነው ? አልገባኝም ፡፡ መረጃም የለኝም ላልከው ግርታ ለፈጠረብህ ድርድር ፣ ቅርበት አለኝ እስካልከን ድረስ ኦስሎና አምስተርዳም ፍላጎቱ እስካለኽ ድረስ ብዙም ስለማይራራቁ ዉነቱን አውጥተኽ ታሳየን ነበር ፡፡ ኦቦ ሌንጮ ለታ ደግሞ ለቡርቃ ዝምታህ ውለታ ሲሉ እጀ- ንፉግ የሚሆኑብህም አይመስለኝም፡፡
ደራሲና ጋዜጠኛ ተስፋዬ ! መቸም እንደቅርበትህም ሆነ እንደጋዜጠኝነትህ ፥ ኦቦ ሌንጮም ሆኑ ፣ ዶክተር ዲማ ነገዎ ኦነግ ውስጥ እንደሌሉ ሳትሰማ የቀረኽ አይመስለኝም ፡፡ ቢያንስ ፊርማና ወረቀቱን አይተናል ብለን ባንመሰክርም – ከኦነግ ተባረዋል ከተባለ ዘመን ባጅቷል፡፡ የቤተ መንግስቱ ሹክሹክታ ውነት ከሆነ ፣ አቶ መለስ ኦህዴድን የሚሸጡት ለቀድሞዎቹ የኦነግ አባሎች እንጂ አስመራ ለሚገኘው ኦነግ አይደለም ማለት ነው ፡፡ እሱም ላይ ቢሆን ገና ኦነግ በሁለት ሰዎች መሪነት የሚነቃነቅ እስከሆነ ድረስ ኦቦ ሌንጮ ለታ እስከአሁንም ድረስ ከነኝህ ሁለት የኦነግ ድርጅቶች ጋር የትሥስር አንጓ እንደሌላቸው ነው የሚነገረው፡፡
የፍትህ ጋዜጣ ባለቤት ተመስገን ደሳለኝ – ’’ህዝብና የተቃዋሚዎች ፓርቲዎች መንታ መንገድ ’’ በሚል ርዕስ በጻፋው መጣጥፍ ላይ እስከዛሬ አገሪቱ በተቃዋሚ ድርጅቶች ፥ ወይም የድርጅቶች መሪዎች ድክመት ላይ ፣ ነቅሶ ያወጣቸውን ነጥቦች ፣በፕሮፌሰር መስፍን ቀጣይነት አስተያየት ቢታከልባትም ፣ አዎ ልክ ነው ወይም የለም ሃሰት ነው የሚል ቀጣይ አስተያየት እስከአሁን በሌሎች ጸሃፊዎች ዙርያም ሆነ የድርጅት ደጋፊዎች ዙርያ አላነበብኩም፡፡ ተመስገን እንዲህ ይለናል ፡፡
’’በነገራችን ላይ ደጋግሜ እንደፃፍኩት ምክንያታቸው ምንም ይሁን ምን የተቃውሞውን ጎራ ለመምራት ወደ አደባባይ የወጡት ፖለቲከኞች በዛጎላቸው ከተሸሸጉት ‹‹ሌሎች ኢትዮጵያውያን›› የበለጠ ‹‹አክብሮት›› ይገባቸዋል። (ይሁንና ግን ሌሎች ኢትዮጵያውያኖች ማለት ምን ማለት ይሆን ? እዚህ ውስጥ የሚመደቡትስ እነማን ይሆኑ ? ከኢትዮጵያ ሌላ ትርፍ አገር ያላቸው ናቸው ወይስ የስርአቱ ምንደኞች ?) ብቻ ከዚህ ባለፈ ክንብንባቸውን ገልጠው ፊታቸውን ያስመቱ ፖለቲከኞቻችን ለእስከአሁኑ አበርክቶታቸው ዋጋ ሊያገኙ ይገባል። በዚህ በኩል ችግር የለም፡፡ ችግር የሚኖረው ያ የአክብሮት ዋጋ በየአመቱ እየተመነዘረ ‹‹መሪ›› በሚል ስም ዛሬም በስልጣናችን እንደተቀመጥን መቀጠል አለብን ሲሉ ነው። ይሄ ወደድናቸውም ጠላናቸውም ትልቅ ችግር ፈጣሪ ነው፡፡ ምክንያቱም አሁን ኢትዮጵያ ያለችበት አጣብቂኝ ከጥቆማና ከአጋላጭ ባለፈ ‹‹አንቂና አደራጅ›› መሪ የሚፈልግበት ወሳኝ ጊዜ ላይ ነውና።’’ ሰረዝ የኔ፡፡
በርግጥ እንደጋዜጠኝነትህ – ኦስሎ በነ – ኤፍሬም ይስሃቅ እንደተጎበኘች ያሰፈርከው ጽሁፍ ትክክል ነው ፡፡ ኤፍሬም ይስሃቅ ኦስሎን ከግር እስከራሷ እያሉ ከርመውባታል፡፡ በቅርቡም እንዳልከው ዶክተር ዲማም ጎብኝተዋታል፡፡ ከኦቦ ሌንጮም ጋር መክረዋል ፡፡ የቤተ መንግሥቱ ሹክሹክታ ለአቶ መለስ ሊሠራ የሚችለው ፣ ኦቦ ሌንጮ ከነሙሉ ክብራቸውና ዝናቸው የታገሉበትን ኦነግ የተባለውን የቀድሞ ድርጅታቸውን ከአስመራ አስነቅለው እንደ ሰባ ሰገል ሰዎች ፊንፊኔ ላይ ለአቶ መለስ ቢያስረክቡ እንጂ እሳቸው ዘወትር ኦስሎ ላይ በጀርባቸው አዝለዋት የሚሄዷትን ቦርሳቸውን ለመለስ ቢያስረክቡት ደስተኛ አይሆንም ፡፡
ችግሩ ምን ላይ መሰለኽ ! ደራሲና ጋዜጠኛ ተስፋዬ ! የፍትሁ ተመስገን እንዳለው ! ችግር የሚኖረው ያ! የአክብሮት ዋጋ በየአመቱ ተመንዝሮ ‹‹መሪ›› የሚለው ቃል ወርዶ ፥ ወርዶ በወጣቱ የኦነግ ደጋፊዎች ዘንድ አልቋልና ነው፡፡ ከዚህ በላይ ምንም የሚጨመር ነገር የለውም ፡፡ የችግሩ ምንጮችን ፣ የፈለግኽውን ሊፕስቲክ ቀባብተህ ፣ የጸጉር ስታይላቸውን ለውጠኽ ፣ አርተፊሻል ጸጉር ጭነኽ ምንይልክ ቤተ መንግሥት ብታቀርባቸው ፣ የችግሩ መፍትሄ አይሆኑም፡፡
በርግጥ ኦቦ ሌንጮ በርዮተ ዓለም ቅርበትና የአማራን ህዝብ በመጥላት ለአቶ መለስ ይቀርቧቸዋል ፡፡ የኢትዮጵያን አንድነት እያለ እስከአሁን የሚዘምረው ኃይል ዘወትር ለኦቦ ሌንጮ ራስ ምታታቸው ነው ፡፡ የሚሰማ’ቸው የሙዚቃ ቃና ’’ የአማራ በላይነት ነው ’’ ፡፡ በዚህ ችግር የተተበተበን ሰው አቶ መለስ ቤተ መንግሥት ወስዶ ቢያስጠጋቸውና ሁለቱንም የሚያስደስታቸውን የሰባራ ሸክላ ሙዚቃ አብሮ ከማድመጥ ሌላ የሚወጣ ምንም አዲስ ነገር የለም፡፡ ከንግዲህ ኦቦ ሌንጮ የኦሮሞን ህዝብ ከወያኔ ጋር ያስታርቃሉ ብሎ መገመት የዋህነት ነው ፡፡
እድሚያቸው ከጡረታ ስላለፈ ፣ የስካንዲኔቪያዋ ክረምትም ብርቱ ስለሆነች አጥንታቸው ድረስ ዘልቃ ስላንዘፈዘፈቻቸው ጸሃይቱን ፍለጋ ፊንፊኔ ቤተመንግሥት ቢያቀኑ አይፈረድባቸውም ፡፡ እንደ ሹክሹክታህ መሠረት ከሆነ ፡፡ ከዚህ በተረፈ ግን! የአቶ ሌንጮ መስራች መሪ የሚለው ቃል በየአመቱ እየተመነዘረ ፣ቁልቁል ስለወረደ ከኦሮሞ ወገኖቻቸው ክብሩ ዝቅ እንዳለባቸው ነው እየታየ ያለው፡፡ ኦነግን ይዞ ገብቶ ውጭ ጉዳይ ሚንስቴርነትን ብለህ የተመኘኽላቸውን በጎ ምኞት እንዲህ በቀላሉ ይሳካላቸዋል ብዬ አላምንም፡፡ ህልም ከአለምን ምናልባት ለኦቦ ሌንጮ ጥሩ ብንመኝላቸው ፣ ለኦሮሞ ህዝብ ’’ መያድ ’’ Ngo ላቋቁምለት ብለው ቢያቀኑ ነው የሚበጀው ፡፡ እሱም ቢሆን ከወያኔ የስለላ መረብ ውስጥ ነጻ አይሆንም፡፡
ደራሲ ተስፋዬ ይልቅስ በቀልድ እያዋዛህ የምትነግረን ምጸታዊ ጆክህ እንዳለች ሆና ! የጥንት የጠዋቱን ሌንጮ ለታ አሁንም በኦነግ ላይ ኃይል አላቸው ብለህ ማመንህ ትንሽ ከመረጃ ውጭ ያስወጣህ ይመስለኛል፡፡ ኦህዴድ በጨረታ ለሌንጮ ለታ ሊሸጥ ነው ያልከን ቀልድ ግን እጅግ ከምር ነው ያሳቀችኝ ፡፡ ድሮ አጎዛ ሰፈር አካባቢ ’’ ነጻ ከብት ’’ የሚባል ሰፈር ነበር፡፡ የጠፉ ከብቶች የሚገኙበት ፡፡ ዛሬ አቶ መለስ አጋሰሶቻቸውን በጨረታ ነው ? ያለ ጨረታ የሚሸጡት ? የጋማዎቹን መንጋጋ አፍ እያስከፈቱ ጥርሳቸውን መሽረፋቸውንና አለመሽረፋቸውን ሳያዩ መቸም አቶ ሌንጮ አይገዟቸውም፡፡ ለመሆኑ ኦህዴድን አቶ መለስ ስንት ጊዜ ነው ገበያ የሚያወጧቸው ? እያልከን ነው በብዕርህ ? እባክህ ስለዳንሰኛው ባጫ ደበሌ አንድ አስቂኝ ቀልድህን ጻፍልን፡፡ በባጫ ብንላጥ ይሻላል ነው የሚሉት የሸገር ልጆች ፡፡
“Meles has to sell his Horse. Lencho wants to buy it.
¨Lencho: Is this horse faithful ?
Meles: Yes, I have sold it 3 times earlier also. It is so faithful, everytime it returned back to me.

No comments:

Post a Comment